ረቡዕ 10 ዲሴምበር 2025

ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን

 የሊቃውንት መፍለቂያ!

ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን


በምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ የሚገኘው ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአጼ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥት በ1466 ዓ.ም እንደተመሠረተ የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ።
የአኹኑ ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ የተሠራው በ1964 ዓ.ም በሁለተኛው የኢትዮጵያ ጳጳስ አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያሪክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ መኾኑን አንዳንድ ታሪክ አዋቂዎች እና የታሪክ ድርሳናት ያስረዳሉ፡፡
ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን ዕድሜ ጠገብ ከመኾኑ ጋር ተያይዞ የመፍረስ አደጋ እንዳይደርስበት በቅርቡ ታሪካዊ ይዘቱን ሳይለቅ እጅግ በአማረ እና በተዋበ መንገድ የጣራ እና ሌሎች የእድሳት ሥራዎች ተደርገውለታል።
የቤተ ክርስትያኑ አጥር ግቢ ለቤተ ክርስትያኑ ተጨማሪ ግርማ ሞገስን አጎናፅፎታል።
በደብረ ገነት ኤልያስ ቤተክርስቲያን ለደብሩ አሥተዳዳሪዎች የሚሰጥ የማዕረግ ስያሜ "ድምሐነ-ገነት"የሚል ሲኾን ትርጓሜውም "የገነት መሐል ወይንም ራስ" ማለት ነው፡፡
ይህ ስያሜ የራሱ የኾነ ትርጓሜ ሲኖረው በሌሎች አብያተ ክርስቲያናት እንደማይሰጥ አባቶች ይገልጻሉ፡፡





በዚህ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ ቀደም ሲል ሰዎች እንደነበሩ በአፈ ታሪክ የሚታመኑ ሁለት ድንጋዮች አሉ፡፡
ድንጋዮቹ በመጠን እና በቅርጽ እጅግ የተለያዩ ናቸው፡፡
ኅብረተሰቡ በተለይም በተለምዶ ሴት እየተባለች የምትጠራውን ድንጋይ ለማንሳት የተለያዩ ሙከራዎችን ያደርጋል፡፡
ድንጋዋን በማንሳትም ኅብረተሰቡ የተለያዩ አንድምታዎችን (ትርጓሜዎችን) ሲሰጥ ይስተዋላል፡፡
የደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተክርስትያን ከጥንት እስከ ዛሬ የዜማ፣ የቅኔ፣ የአቋቋም፣ የመጽሐፍ እና የቅዳሴ መምህራንን በማፍራት ለሀገሪቱ እጅግ ባለውለታ ነው፡፡
ከደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ የዕውቀት መነሻቸውን አድርገው ለዓለም እና ለኢትዮጵያ ባለውለታ የኾኑ እንቁ ሰዎችን አፍርቶ ያበረከተ እና አኹንም በማበርከት ላይ የሚገኝም ነው።
ከእነዚህም ውስጥ፡-
👉ታላቁ ደራሲ እና የቤተ ክህነት ሊቅ ቀኝ ጌታ ዮፍታሄ ንጉሤ


👉 አቡነ ቴዎፍሎስ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ



👉 ታላቁ እና እውቁ የረጅም ልብ ወለድ ድርሰት አባት ክቡር ዶክተር ሀዲስ ዓለማየሁ ይጠቀሳሉ።




በርካታ ሊቃውንትን ያፈራው ቤተ ክርስቲያኑ በአኹኑ ወቅትም በአምስቱ ጉባኤያት በርካታ የአብነት ተማሪዎችን በማስተማር ላይ ይገኛል።



ሐሙስ 16 ኦክቶበር 2025

ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ

 ፍቅር እስከ መቃብር›_ ቴዎድሮስ ካሳሁን


ቴዎድሮስ ካሳሁን(Teddy Afro)
ፍቅር እስከ መቃብር
---------------------//--------------------
ግጥም - ቴዎድሮስ ካሳሁን
ዜማ - ቴዎድሮስ ካሳሁን
ሙዚቃ ቅንብር - አቤል ጳውሎስ /ናደው/
---------------------//--------------------

የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል፣
ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጥል፣
የት ነበር ያረግሁት ቀፎየን ስል ኖሬ፣
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ።
ብራናዬ... አንች የልጅነቴ ጓዴ፣
ተረሣሽ ወይ የእሳት ዙሪያው ተረት ባንዴ፣ ብራናዬ... አንች የልጅነቴ ቀለም፣
እኔ እንዳንች ያጠናሁት ፊደል የለም። ፍቅር የበዛባት ሠማሁ ከማንኩሣ፣
መንናለች ቢሉኝ ቢጫ ልብሥ ለብሣ፣
ሸዋ ከሩፋኤል ስጠብቃት ኖሬ፣
ንቤ ገዳም ገብታ ጎጃም ኖራ ማሬ፣
ሲኖዳ ዮሃንስ ያመት ወዜን ይዤ፣
ጋማ ሽጦ ካሣ ሸኝቶኝ ከወንዜ፣
መጥቼ ከሸዋ ስጠብቃት ኖሬ፣
ለካ ገዳም ገብታ ጎጃም ኖራ ማሬ።(2)
ሀ ብለህ ተው ድገም ሲሉኝ ንሥሃ አባቴ፣
ዋ ብዬ ተማርሁኝ ወይ አለመስማቴ፣
ቀለም ወርቄ ቢሆን የቅርቤ ጓደኛ፣
ፍቅር ለያዘው ሠው ከልካይ የለው ዳኛ።
አሁን በማን ስቄ የልቤን ልካሠው፣
አንዴ በእሷ ፍቅር የተረታሁኝ ሠው፣
የት ርቄስ ባገኝ ከፍቅሯ መሸሻ፣
እሷ ሆና ለኔ ያለም መጨረሻ።
ማር ጧፍ ሆኜ...
ማር ጧፍ ሆና....
ማሬ ማሬ...
ጎጃም ጉራማይሌ፣
ማሬ ማሬ...
ጎጃም ጉራማይሌ፣
ኦሆሆሆ....
ማር ጧፍ ሆኖ... ገባ መቅደሥ፣
ነዶ ለኔ... ፀሎት ሊያደርሥ፣
ዲማ ጊዮርጊስ... ላይ ማንኩሣ፣
ያቺ ወንጌል... ቢጫ ለብሣ፣
ከንግዲማ... ቆብ አስጥዬ፣
እንዳልወስዳት... አባብዬ፣
ሠብልዬ ናት... እማሆዬ፣
ሠብልዬ ናት... እማሆዬ፣
ሠብላለም...
በቢጫው ቀለም፣
ሠብለኣዳም...
ገባሽ ወይ ገዳም፣
ወይ ገዳም....
ገባሽ ወይ ገዳም...
የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል፣ ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጥል፣
የት ነበር ያረግሁት ቀፎየን ስል ኖሬ፣
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ። አ...አሃሃይ...
አ...አሃሃይ...
ብራናዬ... አንች የልጅነቴ ጓዴ፣
ተርሣሽ ወይ የእሣት ዙሪያው ተረት ባንዴ፣ ብራናዬ... አንች የልጅነቴ ቀለም፣
እኔ እንዳንች ያጠናሁት ፊደል የለም። ላሳደገኝ ደብር የሥለት ልጅ ሆኜ፣
ካህን እንዴት ይፍታኝ ያንቺ እሥረኛ ሆኜ፣ በጊዜ ተደፋ የቀለሙ ቀንዴ፣
የኔ ፊደል መሆን ካንቺ አዳነኝ እንዴ። ሣዋህድ ከኖርሁት ቅኔን ከደብተሬ፣
ተሽሎኝ ተገኜ ባላንዲሩ ገብሬ።
ለካ ሠው አይድንም በደገመው መጽሓፍ፣ እንደሠም አቅልጦ ፍቅር ካረገው ጧፍ፣
ለካ ሠው አይድንም በኦሪቱ ገድል፣
ወንጌል ይዞ መጥቶ ፍቅር ካረገ ድል።
ማር ሲገባ ገዳም ድንጋይ ተንተርሶ፣
ጧፉም እንደመናኝ ህይወት ቢጫ ለብሶ፣ ወንጌል መነኮሱ በልጅነታቸው፣
ማር እስከጧፍ ሆኖ ዓለም ቢነዳቸው።
አንች የፍቅር ጥጌ ውድ ነሽ በጣሙን፣ መምጣቴ ነው በቃ እኔ አቃተኝ አሁን፣
አዲስ ዓለም ሆነ ባንቺ ሥል ወጋየሁ፣
እድሌ ሆነና ባጣሽ ተሠቃየሁ።
ማር ጧፍ ሆኜ...
ማር ጧፍ ሆና...
ማሬ ማሬ...
ጎጃም ጉራማይሌ፣
ማሬ ማሬ...
ጎጃም ጉራማይሌ፣
ኦሆሆ......
ማር ጧፍ ሆኖ... ገባ መቅደሥ፣
ነዶ ለኔ... ፀሎት ሊያደርሥ፣
ዲማ ጊዮርጊስ... ላይ ማንኩሣ፣
ያቺ ወንጌል... ቢጫ ለብሣ፣
ከንግዲማ... ቆብ አስጥዬ፣
እንዳልወስዳት... አባብዬ፣
ሠብልዬ ናት... እማሆዬ፣
ሠብልዬ ናት... እማሆዬ፣
ሠብላለም...
በቢጫው ቀለም፣
ሠብለኣዳም...
ገባሽ ወይ ገዳም፣
ወይ ገዳም....
ገባሽ ወይ ገዳም...
ዘንግ ይዛ.....

የቴዲ ጎፈር ‹‹ሰብለ አለም››

 ደረጀ ኅብስቱ derejehibistu

ቴዎድሮስ ካሳሁን ርዕሱ ‹ኢትዮጵያ› በሚለው አልበም ፥ ያልተዳሰሱ ያልተነሱ የኢትዮጵያ ጉዳዮች አሉ ለማለት ያዳግታል። ‹‹ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ›› የምትለዋ የፍቅር እስከ መቃብር ትረካው ግን፥ ለእኔ ጎጃም እስከ መቃብር ሆናብኛለችና፥ ቴዲ አፍሮን በጎጃምኛ ስሙ፥ ቴዲ ጎፈር ብዬ ሰይሜ ጎጃም ላስመንነው ነው፡፡ በጎጃም አካባቢ፥ ፀጉሩን የሚያሳድግ ሁሉ ‹ፀጉሩን አጎፍሯል› ይባላልና፥ ቴዲ ጎፈር እንበለው። መልካም ምናኔ፡፡

‹‹ማሬ ማሬ
ጎጃም ኖራ ማሬ›› እንዴታ! ጎጃምማ ማር ናት፡፡ ማር በንቧ ብዙ ድካምና ልፋት እንዲገኝ፤ ጎጃምም በልፋት በድካም ትገለፃለችና፡፡ የጎጃም ማሯ ትምህርቷና ጤፏ ናቸው፤ በብዙ ድካምና ውጣ ውረድ ገንዘብ ያደርጓቸዋል እንጂ በዋዛ አይቀመሱምና፡፡ ጎጃም ትምህርቷን ልቅሰም ቢሉ፥ ከውሻ ተናክሰው፣ አኮፋዳ ይዘው፣ ደበሎ ለብስውና እከክ ወርሰው፥ በጭንቅ፣ በመከራ ይማሩታል እንጂ፤ አይስ ክሬም እየላሱ፣ ጌም እየተጫወቱ፣ ባክ ባግ ቦርሳ አንግተው አይደለምና፡፡ ጤፍም በአይን ሲያይዋት ትናንሽ ናት እንጅ፥ ትንሽ አንጀትን የምታልብ ድካም ያለባት ሰብል ናት፡፡ መሬቱን ሁለት ሦስቴ ደጋግመው አርስው፣ አለስልሰው፤ ዘር ዘርተው፣ በከብረት አስደቅድቀው፤ ጉልጓሎ ጎልጉለው፣ አረም ሁለት ሦስቴ ታርሞ በብዙ ድካም አድጋ፣ አፍርታ፣ ታጭዳ፣ ተወቅታ ጎተራ ትገባለች እንጅ፤ እንደ ቡና እሸት እየለቀሙ ጎተራ አይከቷትም። ጎጃምማ ማር ናት የምትላስ ወለላ፡፡
ንጉስ ካሌብ ከንግስናው በፍቃዱ ወርዶ ቢመንን የገባው ጎጃም ጣና ገዳም ነበር፡፡ ቅዱስ ያሬድ ሰነፍ ተማሪ እየተባለ በተወለደበት አካባቢ ቢወቀስ ጎጃም ገብቶ የዜማ ሊቅ ሆነ፡፡ ቅዱስ ላሊበላ የገዛ ወንድሞቹ እስከ እየሩሳሌም ቢያሳድዱት ጎጃም ገብቶ፣ በተማረው ጥበብ ሁሉንም አስከነዳቸውና የቅድስና ማዕረግን ተቀዳጅቶ ለዘመናት ምስክር የሚሆኑ ትክል ውቅር ህንፃ ቤተ ክርስቲያኖችን ቆርቁሮልን አልፏል፡፡ የአስራ ስድስተኛው ዘመን ፈላስፋችን ዘርዐ ያዕቆብ እንኳ በተከሰተው ችግር ተማርሮ ሊሰደድ የወደደው ወደ ጎጃም ነበር፤ ምንም እንኳ እንፍራነዝ የሌላ ሃገር መስሎት እንፍራን ሃብቱ ቤት ተጠለልኩ ቢለንም፡፡ ጎጃም ረቂቅ ቅኔ ናት!
‹‹የጸበል ዳር እንኮይ፤ ወንዝ ያወዛት ቅጠል›› የወንዝ ዳር እፀዋት ከልምላሜ፣ ከአበባ፣ ከፍሬ አይለዩም፤ አመት እስከ አመት ከሐመልማል አይታቀቡም፡፡ ሰብለ አለም በቤተሰቦቿ ቤት እንደ ጸበል ዳር እንኮይ፣ እንደ ወንዝ ዳር ቅጠል የፈካች ያማረች ጉብል ነበረች፡፡ ለቤተሰቦቿና ለአካባቢዋ ውበት የምትፈነጥቅ ስጋ ለበስ ሐመልማል፡፡
‹‹ብራናዬ አንቺ የልጅነቴ ቀለም፤
እኔ እንዳንቺ ያጠናሁት የለም››
በእርሷም ልጅነት በባልንጀሮቿም ልጅነት ውስጥ ከህሊና የማትለይ ማራኪ ቀለም፡፡ በልጅነት ዓይናችን ስንመለከት ሁሉም የልጅ ነገር ይሆናልና፤ በልጅነት ትውስታችን ዛሬም ጎጃም ልጅ ናት፡፡ ቀለሟ በህሊናችን ቀልሞ አልጠፋ ያለን የልጅነት መስፈሪያ መለኪያ፣ አለምን መመልከቻ መነጽር ያበጀንባት ብራናችን ጎጃም፡፡ እንደ ማንኩሳው ልጅ በዛብህ፡፡
‹‹ብራናዬ አንቺ የልጅነት ጓዴ
ተረሳሽ ወይ የሳት ዙሪያው ባንዴ››
‹‹ፍቅር የበዛባት ፈልቃ ከማንኩሳ፤
መንናለች ቢሉኝ ብጫ ልብስ ለብሳ››
ማሬ፣ ማሬ ሲላት፤ እንኮይ ሲላት፤ የልጅነት ቀለሜ፣ ጓዴ ሲላት የነበረችውን አሁን በመጠቅለያ ስሟ ‹‹ፍቅር የበዛባት›› ብሎ አመጣት፡፡ ሲማስንላት፣ ሲንገላታላት፣ ሲንከራተትላት የሚኖራት ጎጃሙን ፍቅሬ፣ ፍቅሬ እያለ ሊያሽኮረምማት ይከጅላል። ፍቅር በባህሪው መናኝ ነው፤ ሌላ ጠባይ አይስማማውም፤ ብቻውን ፍቅር ነው፡፡ ቴዲ ጎፈርም መንናለች ቢሉኝ ብጫ ልብስ ለብሳ›› ይላታል ፍቅሩን፤ መናኝ መሆኗን እንደ መርዶ ሁሉ ከሌሎች ነው የሚሰማው፤ ‹‹መንናለች ቢሉኝ›› ይለናልና። መናንያን ብጫ ልብስ ለብሰው፣ ያውም ወይባ ተጎናጽፈው ብርሃናዊ፣ መናኝ፣ ሰማያዊ መሆናቸውን ያሳያሉ፡፡ የቴዲ ፍቅሩ ወደ ጎጃም ያስመነነችው ብጫ/ወይባ አስለብሳ ነው፡፡ ሰብልዬ፣ ሰብልዬ እያለ ሲያንቆለጳጵሳት፤ ጎጃም ሰባተኛው ሰማይ ላይ ሰቀለችው፡፡ ‹‹ባሳደገኝ ደብር የስለት ልጅ ሆኜ፤ ካህን እንዴት ይፍታኝ ያንቺ እስረኛ ሆኜ›› እያለ በምድር የፈታችሁት በሰማይ የተፈታ ይሁን የተባሉት ካህናት እንኳን የማላገኝበት ያንቺ ፍቅር የሰባተኛው ሰማይ መናኝ አድርጎኛል የሚለን ይመስላል፤ ቴዲ ጎፈር፡፡ ‹‹ሸዋ ተሩፋኤል›› ይልና በዘዴ አማላጁን ሩፋኤልን ይጠራል፤ ሩፋኤል ፈታሄ ማህጸን ነውና፡፡ ሴቶች በወሊድ ጊዜ ምጥ ሲበዛባቸው ማህጸናቸውን ፈትቶ በሰላም እንዲገላገሉ ያደርጋል፡፡ ቴዲ ጎፈር የጎጃም ፍቅር ጠንቶበት በጭንቅ ሰባተኛው ሰማይ ላይ ሰቅሎታልና፤ ፈታሄ ማህጸን ሩፋኤል የሰማያትን ማህጸን እንዲፈታለት ይማጸነዋል፡፡
‹‹በጊዜ ተደፋ የቀለሙ ቀንዴ፤
የኔ ፊደል ማወቅ ካንቺ አዳነኝ እንዴ››
በድቁና ዘመኑ የጎጃም መኳንንትንና መሳፍንትን አፍ ያስከፈተው ጉብሉ በዛብህ፤ ባልታሰበ አጋጣሚ ፊደል እንዲያስተምራት በተሰጠችው ሰብለ የምትባል ምትሃታዊ ልጃገረድ አቅሉን ስቶ ጨርቁን ጥሎ አበደ፡፡ ‹‹ድጓ መማር መና፤ ማወቅስ ውሃ ዋና›› እንዳለው፣ የውሃ ሙላት ሚስቱን ሲወስድበት ታዛቢ እንደሆነው ደብተራ፤ የበዛብህ ቅኔ ማወቅ ከሰብለ ፍቅር ሊያስጥለው አልቻለም፡፡
‹‹ማሬ ማሬ ጎጃም ኖራ ማሬ›› እንዴታ! ጎጃምማ ማር ናት፡፡ በኦሪት ዘፍጥረት፣ በሙሴ ቃል ኢትዮጵያን የሚከበው ወንዝ የጎጃሙ ግዮን እንደሆነ ተጠቅሷል አይደል፡፡ ይሄው ግዮንም አይደል እንዴ ገነት ከሚያጠጡ አራት አፍላጋት አንዱ ነው የተባለ። ታዲያ ቴዲ ጎፈር፤ ጎጃምን ፍለጋ መንኖ ሰባተኛው ሰማይ አልወጣም የሚል አለ‘ንዴ? ይሄው በራሱ አንደበት እንዲህ ይለናል፡-
‹‹ማር ሲገባ ገዳም ድንጋይ ተንተርሶ፤
እዩት ጧፍ ገዳም ገባ ቢጫ ልብሱን ለብሶ››
ማር ባህሪ የተባለ ጎጃም ድንጋይ ትራሱ፣ ቅጠል ጉርሱ፣ ዳዋ ልብሱ ሆኖ ገዳም ሲገባ ቢያየው፤ እንዲሁም ማር ባህሪ የሆነች ሰብለ ወንጌል ፀብዐ አጋንንትን፣ ግርማ ሌሊትን ተቋቁማ ድንጋይ ተንተርሳ፣ ጤዛ ልሳ፣ ዳዋ ጥሳ ገዳም ገባች፤ የፍቅር ጧፍ የምሆን ቴዲ፤ ከማር ተለይቼ ጧፍ መሆን፣መኖር፣ መብራት መስጠት፣ ብርሃን መፈንጠቅ አይቻለኝምና ጎጃም መንኛለሁ ይለናል። ጧፉ ቴዲ ጎፈር፤ ወይባ ለብሼ ተከተልኩ እያለም አይደል እንዴ፡፡ ምስጢር ለማመስጠር ስፍራ አልበቃው ብሎ እየፏለለ ጎጃም ይገባል፤ ጧፉ ቴዲ፡፡
‹‹ማር ጧፉኔ፣
ማር ጧፉና፤
ማሬ ማሬ፣
ጎጃም ኖራ ማሬ››
‹‹ማር ጧፍ ሆኖ ገባ መቅደስ፤ ነዶ ሌሊት ጸሎት ሊያደርስ›› ማር የተባለው ፍቅር ማርኮኝ፤ ጧፍ የሆንኩት እኔ ቴዲ ተያይዘን መቅደስ ገባን፤ በፍቅር እሳታችን ሌሊት በተባለው ጥላቻ ላይ እንደ ጧፍ ነድደን የምህረትና የቸርነት ጸሎት ከሚደርስበት ሰባተኛው ሰማይ ገነት ገብተን ምልጃ እያቀረብን ነው የሚለን ይመስላል፤ የጎጃሙ መናኝ ቴዲ ጎፈር።
‹‹ሰብልዬ ሰብልዬ ሰብለ አለም ኧረ ቢጫው ቀለም፤ ሰብለ አለም ገባሽ ወይ ገዳም›› በጭንቅ፣ በምጥ፣ በጋር የተያዘ ሰው ህመሙን ቢደጋግም ቢደጋግም ቢጠራው የሚሻለው የሚድን ይመስለዋልና፤ ስሟን ጠርቶ አይጠግበውም፤ ሰብለ ጎጃሙን፡፡ አልያዝ አልጨበጥ ብትለው ‹‹ኧረ ገባሽ ወይ ገዳም›› ይላታል፡፡
‹‹ማሬ ማሬ ጎጃም ኖራ ማሬ›› እንዴታ! ጎጃምማ ማር ናት፡፡ ጎጃሜ ጉብል ልጁን ሲወዳት ሰብለ ይላታል፡፡ መሬት አርሶ፣ ዘር ዘርቶ፣ አረም አርሞ እንደሚንከባከባት ሰብል ሁሉ ‹‹ሰብለ›› ይላታል የሚወዳት ልጁን፡፡ የሃዲስ አለማየሁ የ‹‹ፍቅር እስከ መቃብሯ›› ሰብለ እንዲህ ያለች ሰብል ናት (ሰመሬታ ሰብስቤ የምትባለውን የዩኒቨርሲቲ ጓደኛቸንን በምን እናስታውሳት ታዲያ በዚህ ካልሆነ)፡፡ የተደከመባት፣ የተንከራተቱላት፣ የሚመንኑላት፣ የመነነች ሰብል። ጎጃም ሲመንኑላት ትመንናለች፤ ስትመንን ይመንኑላታል፡፡ በምናኔ በብቸኝነት ተሰልቃ፣ ተደቁሳ፣ የምትጠፈጠፍ እንጎቻ ናት ጎጃም፡፡ ጎጃምን ይበሏታል እንጂ እሳቷን አይጋሯትም፡፡ ‹‹ማሬ ማሬ ጎጃም ኖራ ማሬ›› እንዴታ! ጎጃምማ ማር ናት፡፡ ጎጃም ሽናሻ፣ አገው፣ ሻንቅላ፣ ዴንሳ፣ ስናን፣ ቀራንዮ፣ ጉንድ፣ ጮቄ፣ ሶማ፣ ባሶ፣ ጃዊ፣ ቻግኒ፣ ወንበራ፣ መተከል፣ ወይጦ፣ ደንቀዝ፣ እንፍራንዝም ናት። ‹‹ሳዋህድ ከኖርኩት ቅኔ ከደብተሬ፤ ተሸሎ ተገኜ ባላንዲሩ ገብሬ›› ጎጃም የባለዋሽንት ባላገር፣ የቅኔ፣ የቀለም ውህድ ሃገር መሆኗን ለማሳየት የኛው ቴዲ ጎፈር ስሪት፣ ንጥረ ነገራችንን እያወዳደረ፣ እያነጻጸረ ያሳየናል፡፡ ‹‹ለካ ሰው አይድንም በዖሪቱ ገድል፤ ወንጌል ይዞ መጥቶ ፍቅር ካደረገ ድል›› ይለናል፤ እርሱን ብቻ ሳይሆን ጎጃም፣ ፍቅር፣ ሰብለወንጌል ሁሉንም አሸንፋለችና።
‹‹አንቺ የፍቅር ጥጌ ወርቅነሽ በጣሙ፣
መምጣቴ ነው በቃ እኔ አቃተኝ አሁን፤
ሃዲስ አለም ሆነ ባንቺ ስል ወጋየሁ…›› ይላል ቴዲ፡፡
ሃዲስ ዓለም የማየት ወግ የሚያደርሰን የጨለማውን መገለጥ የንጋቱን ውጋግ የሚያሳየን መሲህ ከጎጃም ያገኘ እየመሰለው፡፡ የቴዲ የፍቅር ጌጡ ጎጃም ወርቅ ከነጣዕሙ የሚያጣጥምባት መሆኗን ያውቃልና፤ ቀድሞ ገና ቀጠሮ ያስይዛታል - ‹‹መምጣቴ ነው በቃ እኔ አቃተኝ አሁን›› እያለ፡፡ የመሲህ መምጫው በጭንቅ በመከራ ነውና፤ ጭንቅ መከራ የሚበዛባትን የጎጃም ማር ለመላስ፣ ከመሲኋ ጋር ቃል ለቃል ለመመላለስ የሚናፍቅ የሚሽቀዳደም ይመስላል፡፡ ‹‹የት ነበር ያረኩት ቀፎዬን ስል ኖሬ፤ ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ›› የክርስቶስን መወለድ በኮከብ ምልክትነት አውቀው ኮከቡ መንገድ እየመራቸው ቤተልሔም በግርግም ለተወለደው ህጻን እንደ ሰገዱ ሰብዐ ሰገሎች (ጎጃሜውን ዘርዐ ደሽትን ጨምሮ) ቴዲም ንብ ተከትሎ፣ ጎጃም ገብቶ የናፈቀውን መሢህ ያገኘ ይመስላል፡፡
ዊንተር ፓላስ የሚባል የሩሲያ አረቄ ያለ መለኪያ እየተቀዳልኝ፤ ከመነንኩበት ሃሳብ ስነቃ፣ ክለብ ዩጎቪያ ውስጥ መሆኔን ተረዳሁ፡፡ ጋባዥ ጓደኞቼ ከእነመኖሬም እረስተውኝ ዳንኪራቸውን እያስነኩት ነው፡፡ የሚዘፈነውም ዘፈን የጃኖ ባንዶች እንደ ሚዳቋ እየተዘለለ የሚናጡበት ነው። ምንድን ነው እዚህ ሃሳብ ውስጥ የከተተኝ፡፡ ምናልባት ቀን በተደጋጋሚ የቴዲ አፍሮ አዲሱ አልበምን ስንሰማ ስለቆየን ይሆናል፡፡ ጩጬው ጓደኛዬ ፊቱ በሙሉ ላብ በላብ ሆኖ እስክስታውን ይለዋል። ፊቱን ፀሐይ አስመስሎ ሌላኛው ጓደኛዬ ዝላዩን ያጦፋል። እንዳሻው የሚምነሸነሸው ሌላው ጓዴ ወለሉ ጠቦታል፡፡ እኔ በእኩለ ሌሊት መሲህ ከጎጃም እጠብቃለሁ፡፡
‹‹ሃዲስ አለም ሆነ ባንቺ ስል ወጋየሁ፤
 የእድሌ ሆነና ባንቺ ተሰቃየሁ
ማር ጧፉኔ፣
ማር ጧፉና፤
ማሬ ማሬ፣
ጎጃም ኖራ ማሬ››


‹‹የገርማሞ ልጅ ተገርሞ ሊያስገርመን?››
(( ደመቀ ከበደ - ማንኩሳ - ጎጃም ))
የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል
ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጠል….
የት ነበር ያረኩት ቀፎየን ስል ኖሬ
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ
ፍካሬና እማሬ ለግጥም ሁነኛ ተቀብኦዎች ናቸው ይላል ፕሮፌሰር ተሾመ ይመር (የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲው የቋንቋ መምህር)፤ ሀሳብህን ስትፈክረው እማሬውን (ኑባሬውን) አታሳጣው መሆኑ ነው፡፡ ቴዲ ፈክሯልም፤ አዕምሯልም፡፡ እንኳን መሃል ሸገር ላደገው እሱ ቀርቶ ከእኔ ጋር ጥጃ ለጠበቀ የጎጃም (በጥቅሉ የክፍለ ሀገር) ሳተናም እንኳይ የሚበላ የዱር ፍሬ መሆኑን ከዘነጋነውና የአማርኛ ቃል ስለመሆኑም የሚጠራጠር አይጠፋም፡፡
‹‹እንኮይ እንኮይ እንኮይ
የኔ ፉርኖ ዳቦ ልግመጥሽ ወይ››
የሚል ቆየት ያለ ተወዳጅ ዜማ በኢትዮጵያ ሬዲዮ አዳምጥ ነበር፡፡ በልጅነቴ ምንም የገጠር ከተማ (ሞጣ ቀራኒዮ ባድግም) የትምህርት መዘጋትን ተከትሎ ሰኔ ግም ሲል፣ ሀምሌ ከነደመናው አገሩን ሲወረው ከወንዝ ሙላት ታግለን እንጨት (ጭራሮ ለቀማ) ገጠር ወደ ጫካ ስንሰማራ ትዝ ይለኛል፡፡ በተለይ ሶታነት ሲሰማን በነበረ ጊዜ (በከተምቾው በፈነዳን ጊዜ) የብብታችንን ፀጉር፣ የጉልበታችንን ስር ጭገርና የፂማችንንና ሸንጎበታችንን (የከንፈር የላይኛው ፀጉር) የበለጠ ለማጥቆርና ‹ደርሰናል› ለማለት በምላጭ ለመፈግፈግ እንዲመቸን እንጨት ለቀማ መሄድ የምንናፍቀው ጉዳይ ነበር፡፡
በሁለት ምክንያት የበለጠ እወደው ነበር፤
አንድ - ማንም ሳያይ የጉርምስና ውጤቶቼን ለማየት (የአካላቴን ለውጥ)፣
ሁለት - የዱር ፍሬዎችን ለመብላት፡፡ ሾላ፣ ዶቅማ፣ ዋንዛ፣ እሼ፣ …. እና እንኮይ!!
እንኮይ ቢጫ ቀለም ያለው፣ የቄብ ዶሮ እንቁላል የምታክል ኮምጠጥ የምትል ግን ኮምጣጤነቷ ጣፋጭነቷን የማያግድባት እንደሎሚ ያልጠነከረ ገላ ያላት፣ ልስላሴዋ እንቁላል የሚመስል ግን ፍፁም ክብ የሆነች ፍሬ ነች፡፡
እንኮይ በገጠሩ ዘመዶቼና ለእንደኔ አይነቱ ገጠሬነት ናፋቂ ለጎረምሳው የፍቅር ስጦታ፣ ለጎልማሳው የሶታነቱ ትዝታ ናት፡፡
በእንጨት (ጭራሮ) ለቀማ ጊዜ ጎረምሳና ኮረዳ አንድ ላይ ቢሄዱ ነውር የለበትም፤ አንድ ላይ ቢለቅሙም እንደዚያው፡፡ የተፈቀደ የፍቅር መጀማመሪያ ሁነት ነው የሚመስለን፡፡ ከየዛፉ ቆርጠን፣ በአኮፋዳችንና በየኪሳችን ጠርቀን ካጠራቀምን በኋላ ለየከጀልናት ደበቅ እያረግን እንሰጣለን፡፡ በጄ ካለችና ልቧ ከከጀለ ትቀበላለች፤ ካልሆነም አትቀበልም፡፡
እንኮይ ግን እንደዶቅማ ቶሎ አይገኝም፡፡ በእርግጥ ከአካባቢ አካባቢ ካልተለያየ በቀር እኛ ዘንድ ውድ ነበር፡፡ ውድነቱን እንወደው ነበር፤ ለፍተን ደክመን ስናገኘው ለወደድናት የምንሰጠው ውድ ነገር ነበርና፡፡
አሁን የገርማሞ ልጅ
‹‹የፀበል ዳር እንኮይ ወንዝ ያወዛት ቅጠል
ተሸፍና ዋርካ ከልሏት የዛፍ ጠል›› በሚለው ስንኙ
‹‹የፀበል ዳር እንኮይ…›› ሲል በፍቅር እስከ መቃብር ውስጥ በዛብህ ለሰብለወንጌል ፍቅር ውዴታውን ከእንኮይ ጋር ማዛመዱ በፍካሬም በእማሬም ሰምሮለታል፤
‹‹ወንዝ ያወዛት ቅጠል›› ሲላት ደግሞ ያች የፊታውራሪን ወተትና ቅቤ እየጠጣች ያደገች ኮረዳ ትምቡኬ ገላዋና ጉንጯ በዓይነ ህሊናችን እንድትመጣ ‹‹ምስለ ክሰታውን›› ሰማይ አድርሶታል፤
በዚያም ላይ ዓባይ ጎጃምን እንደመቀነት ዞሯታልና ወዲያውም በገጠር ቀዬዎች ዓባይ ዓባይነቱን (ላልቶ) ብቻ ሳይሆን ፀበልነቱን የሚቀበሉትም ባላገሮች አሉና ባህላዊ እሴቱን (ፎክሎሩን) አጢኖታል ያስብለዋል፤
‹‹ተሸፍና ዋርካ…›› ብሎም ያሳምረዋል፡፡ በፊውዳሉ የነፊታውራሪ ዘመን ‹‹ክብር›› እንደ መርግ ለሚጫናቸው መሸሻ ሰብለ ከእልፍኝ የማትወጣ ብትሆን ቁብ አይባልም፡፡ በዛብህ መሸሻና መሸሻነታቸው ከዋርካ ቢገዝፈው፣ ዘመኑ ከመርግ ቢከብደው፣ ፍቅር ባፈዳው ኮስማና ገላውና ጢቢኛ ልቡ የሚቻለው አይደለም፤ እንደዋርካ ትልቅ ዛፍ የለም፡፡ እንደ ዋርካ ረጅም ዕድሜ የሚቆይም እንዲያው፡፡ በዚያ ላይ የጊዜው ባለጊዜ ነበሩ ፊታውራሪ፡፡
‹‹ተሸፍና ዋርካ…›› ይለንና ‹‹ከልሏት የዛፍ ጠል›› ን ሲደግመው ይህ ድጋሜ ልቀቱን ያረቀዋል፡፡ ትልቁ ዋርካ በስሩ ያሉትን ዛፎች ሁሉ ደቃቃ ያደርጋቸዋል፡፡ ዋርካ ግንዱ ብቻ ሳይሆን ቅርጫፉም ሰፊ ነው፡፡ ስለዚህ እንኳን በዝናብ ጊዜ በፀሀይ ወቅትም ጥላው ይቀዘቅዛል፤ ሲዘንብ ከየቅጠሎቹ የሚረግፈው ጠፈጠፍ (ጠል) እንደጤዛ ቶሎ አይረግፍም፤ ጥላውም ጠሉም ቀስ ያለ ነው የዋርካ፡፡ ስለሆነም የዋርካ ስር ተክሎች ሁሉ ቢያድጉም አይጎመሩም፡፡
ሰብለም ለበዛብህ እንዲያ ማለት ናት፡፡ የዋርካው ጠል የስሩን ተክሎች እንደማያስጎነቁላቸው፣ ቢያጎነቁሉም እንደማያስጎመራቸው ሁሉ ሰብለም የ‹‹ዋርካው ቤተሰቧ›› ጠል ተጭኗት ያልጎመራች ነበረች፡፡ የዋርካው ስር ተክሎች ወዲያ በቅርጫፉ፣ ወዲህ በግንዱና በስሩ እንደተቀፈደዱት ሁሉ ሰብለም በፊታውራሪ የታሰረች ‹‹የለመለመች ግን ያልጎመራች ቅጠል›› ነበረች፡፡
የገርማሞ ልጅ ‹‹ፍቅር እስከ መቃብር››ን ሞዝቆታል፤ ተቀኝቶታል፣ ፈክሮታል፣ አዕምሮታልም፡፡ በፈረንጅኛው extratextual art ሰርቶ ነጥሮበታል። ከጥበብ ስራ ላይ ሌላ ጥበብ አውጥቷል።
‹‹የት ነበር ያረኩት ቀፎየን ስል ኖሬ
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ››
ይህ ስንኝ ደግሞ እንድምታው ሸጋ ነው፡፡
ቀፎ እንዳዛሬው ዘምኖ ደጅ ሳይሰጣ፣ በጭራሮና በቀርቀሃ ሳጠራ እየተሰራ ዛፍ ላይ ነበር የሚሰቀል፡፡ ጎጃም የቀይ ማር አዘማሪ፣ አምራችና ጠጃም ነው፡፡ ጠላ እንኳን ተጠምቆ ውብ ሲሆን ‹‹ጠጅ ያስንቃል›› ነው እሚል፡፡
ለጎጃሜ ጤፍ እንጀራው እህሉ ሲሆን ማር ወጡ ነው፤ የዛሬን አያድርገውና፡፡
ባላገር በሞላ በጋውን ያሽሞነሞነውን ቀፎ የበልጉን መብለግለግ፤ የክረምቱን መስገምገም ያይና ከዛፎቹ መሀል ይሰቅለዋል፤ አንዱን ሳይሆን እልፉን፡፡ የቀፎው ብዛት የዛፉን ቅርንጫፍ ያህል ቢሆን ነው፤ ዋርካ፣ ግራር፣ ዝግባና ብሳና የመሰላሰሉ ቅርንጫፈ ብዙ ዛፎች ከሆኑ ባላገር ታድሏል፤ ብዙ ቀፎ ይሰቅላል፡፡
አደይ አበባይቱን ዘፍኖላት፣ መስከረሚቱን አዚሞላት ጥቅምቲቱ ደረስኩ ስትለው ያገሬ ባላገር ‹‹የጥቅምት ማር›› ቆረጣ ይጀምራል፡፡ እየፎከረ እንደሚያጭደው ማኛ ጤፉ እየዘፈነ ጭስ እያጠነ ማሩን ይቆርጣል፡፡
ብዛቱ ‹‹ቀፎዬ የት ነው›› ሊያስብለው ይችላልና በሰበቡ ጎረቤቱ ጋር ሊጣላና በክትክታና ወይራ ሽመል ሊናከት ይችላል፡፡
ማር ለጎጃሜ ጥፍጥናው፣ ውዴታውን መግለጫው ነው፡፡ የወደደውን ‹‹ማር፣ ማርዬ፣ ማርዋ›› ይላል፡፡ ጥር ላይ ልጁን እንኳን ሲድር ‹‹ማሬ›› ብሎ ካልዘፈነ ይነሆልላል፡፡ የእምቦቃቅላ ልጁን የከንፈር ጠብታ (ለሀጭ) እንኳን ‹ማር› ጠብ ይለዋል ነው እሚል፡፡
ወዲህ በምስራቁ ጎጃም በደጀን፣ እነማይ፣ ደብረወርቅ፣ ደብረማርቆስ፣ ጎዛምን፣ ሁለት እጁ እነሴ (ሞጣ ቀራኒዮ) እና መርጡ ለማሪያም እስከ ባሶሊበን ባለው ቀዬ ‹‹ማሬ›› ብሎ ዘፍኖ ባሶ ምት መምታት (እስክስታ መውረድ) የባህሉ አንዱ አካል ነው፡፡
ወዲያም በምዕራቡ አዴት፣ ባህርዳር፣ ቡሬ፣ ፍኖተሰላም፣ ጅጋም አልባሶ መደንከር ወግ ነው ፤ ሁሉም ግን ማሬ ቢል ማር ከቀፎው ቆርጦ ነው፡፡
ማሪቱ ሰብለወንጌልም ከቀፎዋ ወጥታ የት ሄደች ብሎ በዛብህ ዓባይን ተሻግሮ ሲፈልጋት ልቡን ይዛ እዚያው ነበረች - ጎጃም፡፡
በጎጃሜ ንግግር ‹‹የት ኑረህ ነው?›› ካለህ ስፈልግህ ቆየህ፣ የትነበርክ እያለህ ነው ማለት ነው፡፡
ጎጃም ሲናገር ‹‹እዚህ ኑራ!!›› ካለ ‹‹ለካ እዚህ ነበረችና›› እያለ ነው ማለት ነው፤
እናም የገርማሞ ልጅ
….የት ነበር ያረኩት ቀፎየን ስል ኖሬ
ንብ ተከትዬ ባይ ጎጃም ኖራ ማሬ….
ሰብለ የትነች ስል በከበቧት ጀሌዎች ‹‹ንቦች›› የት እንዳለች አወኩ እያለህ ነው፡፡
‹‹ሰብለ ውዴ ጎጃም ነበረች ለካ›› ማለቱ ነው፤ እንጂማ ‹‹ማሬ ማሬ››ን ትዝ ሊያሰኝህም አይደል፤ እረ እሱ እቴ ጎጃሜ ኖሯል - ሸገር መስሎ!!
ለማንቻውም ወረታው ውበትም፣ ቻላቸው አሸናፊም ‹‹ማሬ፣ ማርዘነቤ፣ ማርዋ›› ሲሉ እሷን (ፍቅረኛቸውን) እየፈከሩ ማሩን እያዕመሩ ነው፡፡
ቀፎው የገርማሞ ልጅ ልብ በማሪቱ ሰብለ ሲነሆልል ንቦቹ ከበዋት እነፊታውራሪ ስር ነበረች፡፡
ኧሯ!!! ጎጃም ኖራ ማሩ!!!
ይህንን ጉድማ አሁን አናበቃውም፡፡
እያረፍን እያንዳንዱን ስንኝ እንዘልቃለን፣ በገባን ልክ እንሰልቀዋለን!
ወይ መታደልህ እያልን


ማክሰኞ 24 ጃንዋሪ 2023

ዮፍታሔ ንጉሴ - ተወርዋሪው ኰከብ

ዮፍታሔ ንጉሴ - ተወርዋሪው ኰከብ



በጥበቡ በለጠ
*************
* …..ባለቅኔ፣ መምህር ፣ ጸሐፌ ተውኔት ፣ ዲፕሎማት፣ አርበኛ፣ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት ፣ የመጀመሪያው የኢትዮጵያ ሕዝብ ብሔራዊ መዝሙር ግጥም ደራሲ የነበሩት ቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ ሰኔ 30 ቀን 1939 ዓ.ም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ። በማግስቱም ቀብራቸው በቅዱስ በዓለወልድ ቤተክርስቲያን ተፈጸመ።
የቀኝ ጌታ ዮፍታሔ ንጉሴ አጽም በልማት ምክንያት ከተቀበረበት ቦታ ተነስቶ በትንሽ ሳጥን ተቀምጦ ለሰባት ዓመታት ከቆይ በኋላ ሐምሌ 1 ቀን 2009 ዓ.ም ወደ ትውልድ ቦታቸው ተወሰዶ አጽማቸው ዳግም በደብረ ገነት ኤልያስ ቤተክርስቲያን እንዲያርፍ ተደርጓል። ይህም ማለት ከሞቱ ከሰባ ዓመታት በኋላ መሆኑ ነው።

ታላቁ ባለቅኔ፣ ጸሐፌ-ተውኔት፣ አርበኛ፣ የመዝሙርና የታሪክ ጸሐፊው ዮፍታሔ ንጉሴ፣ ከ70 አመታት በኋላ አጽሙ ካረፈበት ከባለወልድ ቤተክርስትያን ተነስቶ ወደ ትውልድ ቦታው ጎጃም እየተጓዘ ነውሐምሌ 1 ቀን 2009 ዓ.ም ፡፡ ዮፍታሔ ኢትዮጵያ የጥበብ ሊቆችዋን ስትጠራ አንድ… ብላ መጀመሪያ ላይ ከምታስቀምጣቸው ከዋክብቶችዋ አንዱ ነው፡፡ ዋና ከተማዋ በስሙ ትልቅ ሐውልት መገንባት ሲገባት ጭራሽ የዮፍታሔን አጽም ሸኘችው፡፡ እውነት ለመናገር እጅግ ያበሽቃል! ለመሆኑ ባሕል ሚኒስቴርስ ስራው ምንድን ነው? ግን ይህ ብርቅ ኢትዮጵያዊ ጀግና ማን ነው?
ባለቅኔውና ሃያሲው ዮሐንስ አድማሱ ሰኔ 25 ቀን 1961 ዓ.ም ላይ መነን ተብሎ ይታወቅ በነበረው መጽሔት፣ “ተወርዋሪ ኰከብ” የሚል ረጅም ግጥም ፅፏል። ግጥሙን የፃፈው ደግሞ ለዮፍታሔ ንጉሴ ነው። አንዴ ብልጭ ብሎ በሚጠፋው ተወርዋሪ ኰከብ /Shooting Star/ ጋር አመሳስሎት ነው የገለፀው። በትውልድ ውስጥ እንደ ዮፍታሔ አይነት ሰው ብርሃን ሆኖ ወዲያው መጥፋቱን ያስነብበናል።
ብሩሕ ነፀብራቁ
ውበትና ድምፁ አንድነት ተሰምተው
አንድነት ቢቦርቁ
የሚያውቅለት ጠፍቶ
ምስጢሩን አካቶ
ተወርዋሪ ኰከብ በራሱ ነበልባል
በራሱ ነዲድ ተቃጥሎ የጠፋ
ተወርዋሪ ኰከብ በምናየው ሰማይ ነበረ በይፋ
እያለ በቅኔና በውበት የደማመቀ የግጥም ለዛ ለዮፍታሔ ንጉሴ አውርዶለታል። ዮሐንስ አድማሱ እንዲህ ስሜቱ የተነካለት ዮፍታሔ ንጉሴ በኢትዮጵያ የኪነ-ጥበባት ዓለም ውስጥ ደማቅ አሻራ አሳርፈው ካለፉ ባለውለተኞች አንዱ ስለሆነ ነው። እናም ዛሬ ከዮፍታሔ ንጉሴ መንፈስና ተግባራት ጋር አብረን እንቆያለን።
የዮፍታሔ የአባቱ ስም ቄስ ገበዝ ንጉሴ ወልደየሱስ ሲባል፤ እናቱ ደግሞ ወ/ሮ ማዘንጊያ ወልደሔር ተድላ ይባላሉ። ሁለቱም ባልና ሚስቶች ጐጃም ውስጥ ካሉ ባለጠጋ ቤተሰቦች የተወለዱ እንደነበር ታሪካቸው ያወሳል። በትዳራቸውም ምክንያት ሁለት ወንዶችና ሦስት ሴቶችን ወልደዋል። የበኩር ልጃቸው ሴት ነች። ስሟም ትበርህ ንጉሴ ይባላል። ጡት ያስጣላት ዮፍታሔ ንጉሴ ነው። አስቀጣይ ሞሲት ንጉሴ፣ አራተኛዋ ጠጅቱ ንጉሴ፣ መቁረጫው ደግሞ አያሌው ንጉሴ ይባላል።
ዮፍታሔ የተወለደው ጐጃም ውስጥ ደብረኤልያስ ተብሎ በሚታወቀው አካባቢ በ1887 ዓ.ም እንደነበር ሐምሌ 9 ቀን 1939 ዓ.ም የታተመው “ሰንደቅ አላማችን” የተሰኘው ጋዜጣ ያስታውሳል። ስሙንም “ዮፍታሔ” ያሉት በደብረኤልያስ የታወቁ የቅኔና የመጽሐፍ ትርጓሜ መምህር የኔታ ገብረስላሴ እንደሆኑ ታሪኩ ያወሳል። ዮፍታሔ የተወለደባት መንደር ደብረኤልያስ ውስጥ “አመደ ጉባ” ትባላላች።
ትምህርት የጀመረው መምህር አደላ፤ ንጉሴ ዘንድ ነው። ፊደልን፣ ንባብን፣ መዝሙረ ዳዊትን ከተማረ በኋላ የዜማ ትምህርት ቀጠለ። ከዚያም ጾመ ድጓ፣ ምዕራፍን ቀጥሎም ድጓ፣ ከዚያም ቅኔ ቤት ገባ። በወቅቱ በጣም ወጣት ነበር። ትምህርቱን ሲጨርስ መምህር ሆኖ ተመረቀ። በሙያውም ለአምስት ዓመታት ካገለገለ በኋላ የሽማግሌዎችን ሹመት “ቀኝ ጌታ” ተባለ።


ዮፍታሔ እንዴት ወደ አዲስ አበባ መጣ? የሚል ጥያቄ መነሳቱ አይቀርም። እርሱ የመጣበት ምክንያት ሁለት ነገሮች በዋቢነት ይጠቀሳሉ። አንደኛው ንጉስ ሚካኤል ዘንድ መልዕክት ለማድረስ እንደነበር ይወሳል። ንጉስ ሚካኤለ በ1907 ዓ.ም ግንቦት 23 ቀን “ዘ ስልጣኑ ፅሁፍ ዲበ መትከፍቱ ሚካኤል ንጉስ ፅዮን” ተብለው በወሎ፣ በትግራይ፣ በጐጃም ነገሡ። የንጉስ ሚካኤል እናት የትውልድ ሐረግ ደብረኤልያስ ልዩ ስሙ ደልዳል የሚባል ቦታ ስለበር ይሄን ታሪክ ይዞ ዮፍታሔ ወደ ወሎ ሄደ። ዮፍታሔ የሄደው የደብረኤልያስ ሰዎች ኰሚቴ አቋቁመው መልዕክተኞችን ሲልኩ አንዱ በመሆን ተመርጦ ነው። እርሱ ደግሞ የተመረጠው ተናጋሪ (ሪፖርት አቅራቢ) ሆኖ ነው። አልበርት ጀራልድ የተባለው የኢትዮጵያን ሥነ-ፅሁፍ የተመራመረው ፀሐፊ እ.ኤ.አ በ1968 ዓ.ም Amharic Creative Literature በሚል ርዕስ ፅፎታል።
እነ ዮፍታሔ ወደ ንጉስ ሚካኤል ዘንድ ሲሄዱ ቀለብ አልቆባቸው ተቸግረው ነበር። ገንዘብ ማግኛም የሚሆናቸውን ዘዴ ፈጥረው ነበር። ጠንቋይ ሆኑ፣ መፃፍ ገላጭ በመሆን በየአካባቢው ሲደርሱ ሰው “አዋቂዎች” ናቸው እያለ ገንዘብ እየለገሳቸው ቆይተዋል።
ከዚህ ሁሉ በኋላም ደሴ ደርሰው ከንጉስ ሚካኤል ዘንድ መልዕክቱን አቀረቡ። ንጉስ ሚካኤልም ለደብረ ኤልያስ ታቦት መጐናፀፊያ ልዩ ልዩ ንዋየ ቅዱሳትንና መቶ ብር ለገሱ።
ከዚህ በኋላ የዮፍታሔ ህይወት መቀየር ይጀምራል። በ1908 ዓ.ም ወደ ራስ ኃይሉ (የጐጃም ገዢ) ዘንድ ማለትም ደብረማርቆስ ሄዶ ስራ ለመቀጠር ችሎታውን አሳየ። በችሎታውና ባለው የቀለም እውቀት ተደንቆ ተቀጠረ።
ዮፍታሔ ንጉሴ ወደ አዲስ አበባም የመጣበት ምክንያትም ተፈጠረ። ይህም አባቱ ቄሰ ገበዝ ንጉሴ ሲሞቱ እናቱ ወ/ሮ ማዘንጊያ ገና አንዲት ፍሬ ነበሩ። ሥጋወ ደሙ ተቀብለው ነበር የተጋቡት። መመንኰስ ነበረባቸው። ግን አልመነኩሱም። እንደውም አፈረሱ ተባለ። ዮፍታሔም የህዝቡን አሽሙርና አግቦ መቋቋም ተስኖት ወደ አዲስ አበባ ኰበለለ ይባላል። ሌሎች ደግሞ ወደ አዲስ አበባ የመጣው የተሻለ ኑሮ ፍለጋ ነው ብለው የፃፉም አሉ።
ግንቦት ወር 1910 ዓ.ም ዮፍታሔ ንጉሴ አዲስ አበባ መጣ። በቤተ-ክህነት ትምህርት እጅግ በሳል የተባለ አዋቂ በመሆኑ ስራ ለመያዝ ምንም አልተቸገረም። አቦ ደብር ውስጥ ስራ አገኘ። አዲስ አበባ አንድ የጐጃም ሊቅ አገኘች እየተባለ ተወራ። ወዲያው ዝነኛ ሆነ። ቤት ተሰጠው - ያውም ከብላታ መርሴሃዘን ወልደቂርቆስ አዋሳኝ ላይ። ከዚህ ሌላ መተዳደሪያ የሚሆነው አርሲ ውስጥ አንድ ጋሻ መሬት ተሰጠው። ንግስት ዘውዲቱም በ1910 ዓ.ም ካባ ሸልመውታል።
በ1911 ዓ.ም በየካቲት ወር ባየር የሚባል የፈረንሣይ ኩባንያ የወርቅና የብር ማዕድን ለመፈለግ ሲዘጋጅ ስራውን ለመጀመር ካሰለጠናቸው ውስጥ ዮፍታሔና መርሰኤሃዘን (ብላታ) ተመረጡ። የወር ደመወዙም ሰባት ብር ነበር። ከዚያም በሊጋባ ወዳጆ ስር በሊጋባ ጽ/ቤት በ1911 ዓ.ም የጽህፈት ሥራ አገኘ። ደመወዙም በወር 10 ብር ነበር።
ከዚህ ቀጥሎ ደግሞ አንድ አዲስ ነገር መጣ። ነሐሴ 29 ቀን 1916 ዓ.ም ልዑል አልጋ ወራሽ ተፈሪ መኰንን አውሮፓን ጐበኙ። ከአውሮፓ ሲመለሱ ትምህርት ቤቶችን ለመክፈት ወሰኑ። በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ተጨማሪ መምህራን ሲቀጠሩ እሱና መላኩ በጐሰው በወር 30 ብር ተመደበላቸው። በ1918 ዓ.ም ዮፍታሔና መላኩ በጐሰው በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት በአማርኛ መምህርነት ስራ ጀመሩ።
እዚህ ዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት ማስተማር ከጀመረ በኋላ ግጥሞችን እና መዝሙሮችን እንዲሁም ቴአትሮችን “ማምረት” ጀመረ።
ወላድ ኢትዮጵያ ለልጆቿ ብላ
እጅግ ሳይጥሩላት ሳይዘሯት አብቅላ
ስንዴውን ጠብቃ እንክርዳዱን ነቅላ
ስትመግበን አየን በፀሐይ አብቅላ
እያለ መቀኘት የየእለት ተግባሩ ሆነ።
ባለቅኔውና ሐያሲው ምሁር ዮሐንስ አድማሱ፣ መነን መጽሔት ላይ እንደፃፈው ዮፍታሔ ብዙ ዘፈኖችን እራሱ አውጥቶ ነበር። ሙናዬ ሙናዬ፣ የኛማ ሙሽራ፣ አንተ ባላጐዛ ወዘተ የሚሰኙ መዝሙሮችን ደርሷል።
በቴአትር ፀሐፊነትና አዘጋጅነትም የተዋጣለት ሆነ። አፋጀሽኝ የተሰኘችው ቴአትሩና ሌሎችም ስመ ገናና እያደረጉት መጡ። ታላቁ ደራሲ ሃዲስ አለማየሁ በአንድ ወቅት ሲናገሩ “አንድ ጊዜ ጃንሆይ በጣም ከመደሰታቸው የተነሳ ከልዑል አልጋ ወራሽ አንገት ወርቅ አውልቀው ለዮፍታሔ አንገት አጥልቀውለታል” ብለዋል። “የሆድ አምላኩ ቅጣት” የተሰኘው ቴአትር ሲታይ 300 ብር ጉርሻ እና ቴአትሩን ላቀረቡት ተማሪዎች የወርቅና የብር ሰዓት ተሰጥቷቸዋል።
በኢትዮጵያ ውስጥ ቴአትር በማስፋፋትና በማሳደግ ግንባር ቀደም ሆኖ የሚጠቀሰው ዮፍታሔ፣ በ1919 ዓ.ም ሐምሌ 14 ቀን ከብላታ በቀለ ጋር ሆኖ በፈረንጅ አንተማመን የሚል ኀሳብ ያለው ቴአትር ሰርቶ ከብዙ ሳንሱር በኋላ ታይቶለታል።
ቴአትሮቹ ብዙ የመገለጫ ገፅታዎች አሏቸው። አንዳንዶቹን ኀሳቦች የሚወስደው ከመጽሐፍ ቅዱስ ነው። ለዚህም ምስክር የተሰኘው ቴአትሩ ይጠቀሳል። ከዚህ ሌላ ቴአትሮችን ከመዝሙር እና ከህብረ ዝማሬ ጋር ቀላቅሎም የማቅረብ ጥበብ አስፋፍቷል። ከነባራዊው እውነታም እየተነሳ የሚፅፋቸው ቴአትሮች ፖለቲካዊ ጉነጣ ያካሂድባቸው ነበር። ለምሳሌ በ1921 ዓ.ም የፃፈው ቴአትር ኢትዮጵያ ወደኋላ እየቀረች ነው በማለት ምስክር በተሰኘው ቴአትሩ አሳይቷል።
“የኛማ ሀገር የእኛማ ሀገር
ምትሐት ፈጣሪ መልዕክተ ፍጡር
ምን ያለሽ ሞኝ ነሽ ምን ያለሽ ተላላ
ወርቅ ተሸክመሽ መቅረት ወደኋላ”
በኢትዮጵያ ውስጥ ቴአትር በደንብ ተዘጋጅቶ የታየው በ1923 ዓ.ም ጃንሆይ ሲነግሱ ነው። “ጥቅም ያለበት ጨዋታ” የሚለው ይሄው ቴአትሩ በሃይማኖትና በምግባር መካከል ጋብቻ ፈጥሮ የፃፈው እንደሆነ ኤኔሪኰ ቹሪሊ የተባለ የጣሊያን ተመራማሪ ፅፏል።
በ1924 ዓ.ም ሐምሌ 11 ቀን ደግሞ ልዕልት ዘነበወርቅ ከባለቤታቸው ከደጃዝማች ኃይለስላሴ ጉግሣ ጋር ሲመለሱ “ያማረ ምላሽ” የተባለ ቴአትር አሳየ። “የኛማ ሙሽራ” የተባለ እጅግ የደመቀ ዘፈንም አቅርቧል።
በዚሁ ዓመት ለጃንሆይ ልደት “የሆድ አምላኩ ቅጣት” ቴአትር አሳይቷል። የቴአትሩ ሁለት መሪ ገፀ-ባህርያት “በጐ ሰው” እና “ሆድ አምላኩ” ናቸው። በጐ ሰው በንጉሠ ነገስቱ ተመስሎ፣ “ሆድ አምላኩ” በልዑል ራስ ኃይሉ ተመስሎ ነበር የቀረበው።
ንግድ ሚኒስቴር ውስጥ ይሰሩ የነበሩት መሐሪ ካሣ የተባሉ ጓደኛው ስለ ዮፍታሔ ሲመሰክሩ ማስታወሻ ደብተርና እስክሪብቶ ከእጁ አይጠፋም ብለዋል። ዮፍታሔ በ1925 ዓ.ም የቅዱስ ጊዮርጊስ ትምህርት ቤት ዳይሬክተር ሆኖ ተሾመ።
ይህ ፀሐፌ-ተውኔት በ1925 ዓ.ም ህዳር 11 ቀን በኦሮምኛ ቋንቋ “ዳዲ ቱራ” የሚል ቴአትር ፅፏል። ቴአትሩ በኦሮሞ ባህል ላይ የሚያተኩር ነው። ሐምሌ 16 ቀን 1926 ዓ.ም ደግሞ “የህዝብ ፀፀት የእመት በልዩ ጉዳት” የተባለ ቴአትር በዳግማዊ ምኒልክ ትምህርት ቤት አሳየ። ቴአትሩ በሽታ ያለባቸው ሀብታሞች ህመማቸው በሌላ ሰው ላይ ሆን ብለው ሲያሰራጩት የሚያሳይ ነው። ይህን የቴአትር ፅሁፍ ግን እስካሁን አግኝቼው አላነበብኩትም። የት እንዳለም ላገኘው አልቻልኩም።
ዮፍታሔ ንጉሴ ስለ ጀግኖች ኢትዮጵያዊያንም አርበኝነትና ተጋድሎ በመፃፍ የሚታወቅ ባለቅኔ ነው። ከንጉስ ኃይለስላሴና ቤተሰቦቻቸው በተጨማሪ ለታላላቅ ኢትዮጵያውያን ተቀኝቷል። ለምሳሌ ህዳር 26 ቀን 1927 ዓ.ም ወልወል ላይ በተደረገው ጦርነት ፊታውራሪ አለማየሁ መሞታቸውን ሲሰማ የሚከተለውን ቅኔ አቅርቧል።
አለማየሁ ጐሹ እንደቀድሞው ካሣ
አጥንቱን ከስክሶ ደሙን አፍስሶ
ደጃዝማች አፈወርቅ ምድሩን አሳርሶ
አጥንቱን ተከለው፤ ደሙን አለስልሶ
የውጋዴን ዳኛ የውጋዳን ዳኛ
ደከመው መሰለኝ ተሸፋፍኖ ተኛ።
ዮሐንስ አድማሱ ሲገልፅ ጐበዝ ደራሲ ነብይ ነው ይላል። የሚመጣውን ነገር አሻግሮ ማየት የሚችል። ዮፍታሔም ልክ እንደ ደራሲ ተመስገን ገብሬ አይነት ነብይ ነበር። ምክንያቱም ጣሊያን ኢትዮጵያን እንደምትወር ቀደም ሲል ከታያቸው ጠቢባን መካከል አንዱ እርሱ ነው። የጠላትን መምጣት በሚከተለው መልኩ ቀደም ብሎ ጽፎታል።
አትርሱኝ እዘኑ ዘመዶቼ ሁሉ
እኔም ታምሜያለሁ ባሌም ታሟል አሉ።
እንጃ መዳኑን እንጃ መዳኑን
እየቆራረጠ አሞታል ባሌን
ዘወትር ይስቃል አወይ ጥርሴ ሞኙ
ጐፈሬዋን አይተው ዙረው የተመኙ
ዳሩን እንጋባ እያሉ ሲመኙ


የዮፍታሔ ንጉሴን ነብይነት ከመሰከሩት ታላላቅ ኢትዮጵያውያን መካከል ንጉስ ኃይለስላሴ እና ፀሐፌ ትዕዛዝ ወልደጊዮርጊስ ይገኙበታል። ፋሽስቶች ኢትዮጵያን ሲወሩ ከንጉስ ኃይለስላሴ ጋር በመሆን ወደ እንግሊዝ የተጓዙት ፀሐፌ ትዕዛዝ ወልደጊዮርጊስ ሰኔ 16 ቀን 1929 ዓ.ም ለዮፍታሔ ንጉሴ የሚከተለውን ደብዳቤ ፅፈውለታል።
“ወንድሜ ሆይ፤ ምስጢራዊ ንግግርህና ፅህፈትህ ዛሬ አደባባይ ወጣ። መስጢር የለውም። ጊዜ ይገልጠዋል። ይኸውልህ ሁላችንንም የድካማችንን ፍሬ እግዚአብሔር እንዲህ አደረገው” ብለውታል።
ዮፍታሔ ንጉሴ በዘመኑ ልክ እንደ ደራሲ ተመስገን ገብሬ ሁሉ ንግግር አዋቂ ነበር። በ1927 ዓ.ም የሀገር ፍቅር ማኅበር ሲመሰረት በበጅሮንድ ተ/ሐዋርያት እና በሌሎችም አሳሳቢነት ስለ ኢትዮጵያ ፍቅርና አንድነት ንግግር እንዲያደርጉ “ዲስኩረኞች” ተመረጡ። እነዚህም፤ ዮፍታሔ ንጉሴ፣ ተመስገን ገብሬ፣ ወልደጊዮርጊስ ወልደዮሐንስ፣ ደምስ ወ/አማኑኤል፣ መላኩ በጐሰው፣ አስፋው አንዳርጌ፣ መርስኤ ሀዘን ወ/ቂርቆስ፣ አበበ ገመዳ፣ መንገሻ ከፈለ፣ ኃይለገብርኤል ነገሮ ነበሩ። እነዚህ ሰዎች የኢጣሊያ ወረራ ከመምጣቱ በፊት ህዝቡ ነቅቶ ሀገሩ ኢትዮጵያን እንዲጠብቅ ያስተማሩ የታሪክ ባለውለተኞች ናቸው። ዮፍታሔም ከነርሱ መካከል አንዱ ነው።
ይህ የኪነ-ጥበብ ሰው፣ ኢትዮጵያን በጀግኖቿ ተመሳሌነት በአንድነት ለማስተሳሰር ሲል እጅግ ውብ የሆነ ግጥምም ፅፏል። ይህ ግጥም ርዕሱ “አጥንቱን ልልቀመው” የሚል ነው።
አጥንቱን ልልቀመው መቃብር ቆፈሬ
ጐበናን ተሸዋ አሉላን ከትግሬ
ስመኝ አድሬያለሁ ትናንትና ዛሬ
አሉላን ለጥይት ጐበናን ለጭሬ
ጐበና ሴት ልጁን ሊያስተምር ፈረስ
አሉላ ሴት ልጁን ጥይት ሊያስተኩስ
አገሬ ተባብራ ታልረገጠች እርካብ
ነገራችን ሁሉ የእንቧይ ካብ የእንቧይ ካብ።
የሀገር ፍቅር ስሜትን በኢትዮጵያዊያን ደም ውስጥ በማስረግ ከሚታወቁት የኢትዮጵያ ጠቢባን መካከል አንዱ የሆነው ዮፍታሔ ንጉሴ በ1928 ዓ.ም ጐበዝ አየን የምትሰኝ መጽሐፍ አሳትሟል። በዚህች መፅሐፍ ውስጥ፤ ሰው ለሀገሩ፣ ለነፃነቱ፣ ለክብሩ ቢሞት እንደሞተ አይቆጠርም ይላል።
“ሕይወቱን ጠብቆ የሞተ ላገሩ
በሕይወት ይኖራል ነፃነቱ ክብሩ”
የኢጣሊያ ወረራ
ፋሽስት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ስትወር በመጀመሪያ ያደረገችው ለሀገርና ለወገን ተቆርቋሪ የሆኑ እንደ ዮፍታሔ ንጉሴ ያሉትን ሰዎች ማጥፋት ነበር። ቤት ለቤት እየዞሩም አሰሳቸውን ቀጠሉ። ሐምሌ 10 ቀን 1928 ዮፍታሔን ፍለጋ ቤቱ መጡ። ቤቱን በርብረው በርካታ ሠነዶቹን ወሰዱበት። እሱ ግን በአጋጣሚ አልነበረም። በብሽቀት ጐረቤቱን አለቃ መርሻን ገድለው ሄዱ።
ዮፍታሔ በወቅቱ ያስቸገሩት ለጣሊያን ያደሩ ባንዳዎች ነበሩ። “እኔ የምሸሸው ከኢጣሊያኖች ሳይሆን ከእኛው ዜጐች ነው” በማለት በወቅቱ ዮፍታሔ ተናግሯል። በዚህም የተነሳ ራሱን ቀያይሮ በማይታወቅበት ሁኔታ ከተማው ውስጥ ይዘዋወር ነበር።
ጢሙን አሳድጐ፣ የቄስ ልብስ ለብሶ፣ ጢሙም ገረጃጅፎ አድጐ ከተደበቀበት ወጥቶ ሲሄድ በፍፁም አይታወቅም ነበር። ብላታ መርሴሃዘን መንገድ ላይ አግኝተውት አላወቁትም ነበር። እሱ ግን ዮፍታሔ ነኝ ብሎ ነገራቸው።
አንድ ቀን ደግሞ የቄስ ልብስ ለብሶና ጠምጥሞ፣ መስቀል እያሳለመ፣ ማንነቱ ሳይታወቅበት አዲስ አበባን ለቅቆ በአቃቂ በኩል ወደ አዋሽ ሄደ። አመለጠ። አዋሽም ደጃች ባልቻን አገኘ። አብረው ሆነው ጣሊያንን ወጉ። ባንዳው ግን አስቸገራቸው።
በኋላ ወደ ጎሬ መጓዝ ጀመረ። ጉዞው አደጋ ያለው መሆኑን ሲያውቅ የባህታዊ ልብስ ለብሶ አንዲት ቤተ ክርስቲያን ተጠግቶ መቃብር ቤት ውስጥ ማደር ጀመረ። በኋላም ማስወራት ጀመረ። “አዋቂ ነው፤ ጥንቆላውም መሬት ጠብ አይልም፤ የተናገረው ሁሉ እውነት ነው” ተባለለት። እናም ጆቴ የተባለው እዚያ አካባቢ የነበረውን የኢጣሊያን የጦር አዛዥን “ነብይ” ሆኖለት ጠነቆለለት። “ጆቴ፤ በኢትዮጵያ ላይ ትነግሳለህ፤ ይቀናሃል” አለው። ጆቶም እጅግ ደስ ብሎት ለዮፍታሔ የሚፈልገውን ሁሉ እንዲደረግለት አደረገ። ዮፍታሔ ደግሞ ዋናው አላማው ወደ ጐሬ መሄድና የትግል ስልቱን መቀየር ነበር። እናም ጐሬ ደርሶ ለመምጣት ፈቃድ አግኝቶ አመለጠ። ከዚያም ሱዳን ገባ።
ካርቱም ከገባ በኋላ በርካታ ተግባራትን ማከናወን ጀመረ። በተለይ ደግሞ ልዩ ልዩ ድርሰቶችን እየፃፈ ወደ ለንደን ይልካል። እዚያም የነበሩት ጃንሆይ፣ ብላቴን ጌታ ኅሩይ ወ/ስላሴ እና ፀሐፌ ትዕዛዝ ወልደጊዮርጊስ ያነቡለት ነበር። እንደውም በአንድ ወቅት ጃንሆይ የሚከተለውን ደብዳቤ ወደ ዮፍታሔ ፃፉ።
“በየጊዜው የምትልከው ደብዳቤ እየቀረበልን ተመልክተነዋል። ባጭር ባጭሩ እያዘጋጀህ ላከው። የትካዜ መዝሙር ልብ ይነካል” /መጋቢት 19 ቀን 1930 ዓ.ም/
ዮፍታሔ ንጉሴ የልቦለድ ድርሰት እንደፃፈ ቢናገርም፤ እስከ ዛሬ ድረስ የት እንዳለ አይታወቅም። ካርቱም ላይ “አፋጀሽኝ” የተሰኘውን ድንቅዬ ቴአትሩን ፅፏል። ቴአትሩ ኢትዮጵያ እንዴት በጠላት እጅ እንደወደቀችና እንዴትስ እንዳዳነች ከአንዲት የታመመች ሴት ጋር አመሳስሎ ፅፎታል። በመታመሟ እና በመዳኗ መካከል ያለውን ድርጊት በማሳየት የጊዜውን የፖለቲካ ሁኔታ የሚገልፅ ቴአትር ነው።
ከዚህ ሌላ “ደብረጽዮን” የተባለ መጽሐፍ ፅፎ ነበር። ግን የት እንዳለ አይታወቅም። “ዐመተ ምህረት” የሚለው መጽሐፉም ፀሐፌ ትዕዛዝ ወ/ጊዮርጊስ ዘንድ ተቀምጦ ነበር ይባላል። እሱም አልተገኘም። ስደተኞች ተስፋ እንዳይቆርጡም “በለስ ለመለመች” እና “ጐሀ ፅባህ” የተባሉ መዝሙሮች ደርሷል።
ዮፍታሔ አደገኛ ሰላይ ሆኖ ለሀገሩ ኢትዮጵያ አገልግሏል። ከሱዳን ወደ ኢትዮጵያ ራሱን በልዩ ልዩ መልክ እየቀየረ በመምጣት ከአርበኞች ጋር ተገናኝቶ እና የሚፈልገውን መልዕክት አድርሶና ተቀብሎ ወደ ሱዳን ይመለስ ነበር። ለጃንሆይም መልዕክት ያስተላልፍ ነበር።
ይሄ ሁሉ መከራ አልፎ የጣሊያኖች ግብዐተ መሬት ይፈፀም ጀመር። አርበኞች ድል በድል ሆኑ። የጣሊያኖች ምሰሶ ሲናድ የተሰደደው የኢትዮጵያ መንግስት ተመልሶ መምጣት ጀመረ። ጃንሆይ ከእንግሊዝ ወደ ካርቱም ከዚያም ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ዮፍታሔ የጉዞ ማስታወሻ ፀሐፊ ሆኖ አብሮ መጣ።
በዚህም ጉዞ ወቅት “ደሙን ያፈሰሰ” እና “ተጣማጅ አርበኛ” የተሰኙ የሰንደቅ ዓላማ መዝሙሮች ደረሰ። ኢትዮጵያ ከመጡ በኋላ በድል ማግስት “አፋጀሽኝ” ቴአትሩን አሳየ። በዚያን ጊዜ ተዋናዮቹ 30 ነበሩ። 10 አረንጓዴ፣ 10 ቢጫ፣ 10 ቀይ ልብስ ለብሰው መስከረም 3 ቀን 1934 ዓ.ም አሳዩ። ቴአትሩ የኢትዮጵያ የነፃነት መንፈስ መገለጫ ሆኖ ናኘ።
ለሀገሩ ይህን ሁሉ መስዋዕትነት የከፈለው ዮፍታሔ ከነፃነት በኋላ ስራ እንኳን ሳያገኝ ከአንድ ዓመት በላይ ቁጭ አለ። ባንዳዎች እንኳን ሳይቀሩ ስራ ተሰጥቷቸው ነበር። ያ ሁሉ ተስፋው ከንቱ ሆነ። ሀዘን ገባው። እውቀቴ ችሎታዬ አንሶ ነው? ብሎም አሰበ። አገልግሎቴስ አጥጋቢ አልነበረም ማለት ነው? ይል ጀመር። የባንዳዎችን ሹመት ሲያይ የሚከተለውን ገጠመ።
ለጌሾ ወቀጣ
ማንም አልወጣ
ለመጠጡ ለመጠጡ
ከየጓዳው ወጡ
ከዚህ በኋላ ሥነ-ጥበብ ሚኒስቴር ውስጥ ስራ ተሰጠው፤ በወር ከ150 ብር ደመወዝ ጋር። ግን አልሰራም አለ። ሐምሌ 16 ቀን 1934 ዓ.ም “እያዩ ማዘን” የተባለ ቴአትር ፃፈ። ቴአትሩ ደግሞ ከፍተኛ ብስጭቱን የገለፀበት ነበር።
ጌታዬ የኔ ጌታ ጌታዬ
በመስቀልህ ባርከኝ
በስልጣንህ ባርከኝ
ዕድሌንም ባርከው
ተመለጠ ራሴ እየቆጨኝ ባከው።
ይህን ቴአትር የተገነዘቡት አፄ ኃይለስላሴ ውሣኔ ሰጡ። ወዲያው ጥቅምት 18 ቀን 1935 ዓ.ም ዮፍታሔ ንጉሴ የሕግ መወሰኛ ምክር ቤት ምክትል ፕሬዝዳንት አድርገው ሾሙት። ከዚህ በኋላም “ዕርበተ ፀሐይ” የተሰኘውን ቴአትሩን ፅፏል። ቴአትሩ የልዕልት ፀሐይ ኃይለስላሴን ሞት ምክንያት በማድረግ የተፃፈ ነው።
ዮፍታሔ ንጉሴ ሦስት ትዳሮችን በየጊዜው መስርቷል። ወ/ሮ ጥሩነሽ ደባን፣ ወ/ሮ ሙሉወርቅ ጠናን እና የመጀመሪያዋ የሴት ጋዜጠኛ የነበሩትን ደራሲ ሮማንወርቅ ካሳሁንን አግብቷል። ትዳር የቀያየረ ባለቅኔ ነበር።
ዮፍታሔ በኢትዮጵያ ኪነ-ጥበብ ዓለም ውስጥ አጭር የሆነ ጊዜ ቢቆይም፤ አብርቶ ያለፈው ብርሃን እጅግ ደማቅ ነበር። በርካታ ጉዳዮች ላይ ፅፏል። ለምሳሌ “ከማይጨው እስከ ደብረማርቆስ” የተሰኘ የታሪክ መጽሐፍ አበርክቶልናል። “ጐበዝ አየን”፣ “አመተ ምህረት”፣ “ደብረ ጽዮን”፣ የተሰኙ አራት መፃህፍትን አሳትሟል። በቴአትር ዘርፉ ደግሞ 17 ቴአትሮችን ፅፎ እና አዘጋጅቶ እንዲሁም አሳይቶ አልፏል። ከ20 የሚበልጡ መዝሙሮችን ደርሷል። የኢትዮጵያ ህዝብ መዝሙር ደራሲም ነበር። በቅኔ፣ በዜማ፣ በመድረክ ንግግር ወዘተ ከፍተኛ ተሰጥኦውን አሳይቷል። አያሌ ደብዳቤዎችና የጉዞ ማስታወሻዎችን ፅፏል። እነዚህ ቀሪ ስራዎቹ ዛሬም ስለ እሱ ይመሰክራሉ።
ይህ ታላቅ ኢትዮጵያዊ ሰኔ 30 ቀን 1939 ዓ.ም ድንገት አሞት ሐኪም ቤት ሄዶ መርፌ ተወግቶ ተመልሷል። ህመሙ ከባድ ስላልነበር ከስራው አልቀረም። ማታም ከጓደኛው ከአቶ መሐሪ ካሣ ቤት ደህና ሲጫወት አምሽቶ ወደ ቤቱ ገብቶ ተኝቷል። ሆኖም ጧት ሰራተኛው ቁርስ ሰርታ ብትጠብቀው አልመጣም። ታላቁ የኪነ-ጥበብ ሰው ሰኔ 30 ቀን 1939 ዓ.ም በ52 ዓመቱ እስከወዲያኛው ተሰናብቶናል። አንዳንዶች የተመረዘ ነገር ተሰጥቶት ነው የሞተው ይላሉ። ሌሎች ደግሞ የከሰል ጭስ አፍኖት በማለት ይገልፃሉ። ሞቱ ግን ምስጢር ነው!
ሰውን ሰው ቢወደው አይሆንም
እንደራስ
ታመህ ሳልጠይቅህ መቅረቴን
አትውቀስ
ባውቀው ነው ተመጣሁ
እንደማልመለስ
ይማርህ መሐሪው እስክመጣ
ድረስ።


ይህን የዮፍታሔን ታሪክ ለመፃፍ ያገለገሉኝ ሰነዶች፤ ዮሐንስ አድማሱ፣ ፕ/ር ሪቻርድ ፓንክረስት የፃፏቸው መፅሀፍት፣ ሙሉጌታ ስዩም 1964 ዓ.ም የፃፈው ታሪክ፣ ዶ/ር አምሳሉ አክሊሉ 1976 ዓ.ም ያዘጋጁት፣ ተስፋዬ ገሠሠ የፃፈው የቴአትር ታሪክና ራሱ ዮፍታሔ የፃፋቸው ታሪኮች ናቸው።

ሐሙስ 17 ኖቬምበር 2022

የቅኔ ‹‹ዩኒቨርሲቲው›› ዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም

 


አንዳንዶች ‹‹የኢትዮጵያ ቅኔ ዩኒቨርሲቲ ነው›› ይሉታል። ምክንያቱም ተማሪው ከመምህሩ ጋር ሰምና ወርቁን እያስማማ ሲዘርፍ ማስተዋል በቦታው የዕለት ተዕለት ተግባር ስለሆነ። ሌሎች ደግሞ የፍቅር እስከ መቃብር ታሪክ እትብት የተቀበረበት ስፍራ ነው ይሉታል። ምክንያቱም የሚያውቁት የሐዲስ አለማየሁ የፍቅር እስከመቃብር ድርሰት ታሪክ ዋነኛ መቼት በመሆኑ ነው። ዲማ ከአዲስ አበባ በደጀን ታጥፎ ወደ ሞጣ በሚጓዘው መንገድ ከብቸና ከተማ በስተ ምስራቅ ይገኛል። ምቹውን የደጀን እና ቢቸና አስፓልት መንገድ እንዳጠናቀቁ ምእራባውያን ‹‹አፍሪካን ማሳጅ›› እያሉ የሚሳለቁበት ዘጠኝ ኪሎ ሜትር የውስጥ ለውስጥ የጠጠር መንገድ ይቀበሎታል።

 የውጭ ጎብኚዎች ይህን ስም ያወጡለት በጉዞው ላይ ምቾት እየነሳ እና እያንገራገጨ ከተሽከርካሪው ወንበር ጋር ስለሚያፋትጋቸው ነው። ውብ የባህል፣ የሃይማኖት እንዲሁም የተፈጥሮ ቦታ አጣምሮ ወደያዘችው ዲማ መጓዝ ለሚሻ ሰው ይህ ትንሽ ችግር እንቅፋት እክል እንዳይሆንበት ማሰቡ መልካም ነው። መንገዱ ለቱሪስት በተለይም ለህጻናትና አረጋውያን የማይመች መሆኑን ልብ ይሏል። ‹‹ዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም›› በምስራቅ ጎጃም ዞን እነማይ ወረዳ ከሚገኙት ስመ ጥር የቱሪስተ መዳረሻዎች መካከል አንዱ ነው፡ ፡

 እነማይ ወረዳ በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በምስራቅ ጎጃም ዞን ከሚገኙ 21 ወረዳዎች ውስጥ አንዱ ነው። እነማይ ከአዲስ አበባ በ265 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል።

 ከባህርዳር ደግሞ በ222 ኪሎ ሜትር ርቀት አለው። ዲማ ጊዮርጊስ ገዳም በአካባቢው ትልቅ የቱሪዝም መዳረሻ መሆኑ ታምኖበት የባህልና ቱሪዝም ባለሙያዎች መጠነኛ የማስተዋወቅ ስራ እያከናወኑበት ይገኛል። ይሁንና ታሪካዊውን በይበልጥ ታዋቂ ያደረገው የሐዲስ አለማየሁ ድርሰት መሆኑ የማይካድ ነው።

የገዳሙ ትርጓሜ

የገዳሙ መጠሪያ ስም በቀድሞ ዘመን ‹‹ደብረ ድማህ›› ይባል የነበረ ሲሆን ከጊዜ ቆይታ በኋላ ስያሜው ወደ ‹‹ዲማ›› ተለወጧል። ታሪክ አዋቂ አባቶች እንደሚሉት ከሆነ ደብረ ድማህ ማለት ከግዕዝ የተወረሰ ቃል ሲሆን ትርጓሜውም (ራስ፣ የሁሉ የበላይ ወይም ጭንቅላት) እንደማለት ነው። ከዚህ ትርጓሜ መረዳት እንደሚቻለው ቦታው በጊዜው የጎጃም ማዕከል እንደነበረ ነው። የገዳሙ መጠሪያ ስም ‹‹ደብረ ዲማ›› ሲሆን በትርጓሜው መሰረት ገዳሙ የሁሉ የበላይ መሆኗን ለማመላከት የወጣ መሆኑን መገንዘብ ያስችላል። በሌላ በኩል ዲማ ማለት ቀይ ማለት እንደሆነ የሃይማኖት አባቶች ይናገራሉ። በጊዜው አንድ ትልቅ ቀይ ዛፍ በቦታው ስለነበረና ስሙም ከዚህ የተወሰደ መሆኑን ለማመላከት እንደሆነም ይነገራል፡፡

 ዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም የተመሰረተው በአፄ አምደ ጽዮን ዘመነ መንግስት በ1297 ዓ.ም ነው። ከአፄ ይስሃቅ ዘመነ መንግስት ጀምሮ ደግሞ በገዳምነት ተሰይሞ፤ በሚሰጠው ትምህርት አማካኝነት ዝናው የናኘ ሊሆን በቅቷል። ዲማን የመሰረቱት አባት አባ በኪሞስ የተባሉ ሰው ናቸው። በጎጃም እየተዘዋወሩ ወንጌልን በመስበክ እየጠመቁ ሳለ አንድ ቀን ከአማንያን ብዛት የተነሳ የማጥመቅን ስራ ሳይጨርሱ ጀንበር ትጠልቅባቸዋለች። ይህ ሲሆን አምላክን ይለምኑታል። ብርሃንም ወርዶላቸው ስርዓተ ጥምቀቱን ይፈፅማሉ። ይሄ ተእምር እንዲፈፀም ያስቻሉት አባት ከዚያ ጊዜ በኋላ ስማቸው ተከስተ ብርሃን እንደተባለ እና በገዳሙ ታሪክ ትልቅ ቦታ እንደተሰጣቸው በድርሳናት ላይ ተፅፎ እንደሚገኝ መረጃዎች ይጠቁማሉ።

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የሀዲስ ኪዳን ሥርዓተ ህግ መሠረት አራት የአስተዳደር ሥርዓቶች አሉ፡፡ እነርሱም ደብር፣ ገዳም፣ ገዳም ወደብር እና ገጠር በመባል ይታወቃሉ። የዲማ ጊዮርጊስ አስተዳደር ሥርዓት ደግሞ ገዳም ወደብር የሚባለው ዓይነት ነው። ባህሪውም ስጋዊና መንፈሳዊ ገጽታ ያለው ሲሆን የገዳምነትንና የደብርነትን ስራ አጣምሮ ይዟል። እንደገዳምነቱም በመነኩሴ ብቻ ነው የቅዳሴ ሥነሥርዓት የሚካሄደው። አስተዳደሩንም በበላይነት ይመሩታል።

እንደ ደብርነቱ ደግሞ ስጋዊ ህይወት የሚመራበት በመሆኑ ስጋዊ የአስተዳደር ሥርዓትም ጐን ለጐን ይካሄድበታል፡፡ የዲማ ገዳም ወደ ብር የሰበካ ጉባኤ በበላይነት የሚተዳደረው በመነኩሴ ሲሆን መጠሪያ ማዕረጉም ‹‹ርዕሰ መምህር›› ይባላል። መምህሩ የሚመረጡት በህዝብ ነው፡፡ የሃይማኖት ህፀፅና ነውር ካልተገኘባቸው በስተቀር እስኪሞቱ ድረስ ወንበራቸው የፀና ነው። አሁን ገዳሙን የሚመሩትና የሚያስተዳድሩት መምህር አባ ወልደ እየሱስ የሚባሉ ዕድሜያቸው በ60ዎቹ የሚገመት መነኩሴ ናቸው።

የገዳሙ ቅኝት

ዲማ ጊዮርጊስ ከትንሿ የገጠር ከተማ በስተደቡብ ከደልዳላ ስፍራ ላይ በአረንጓዴ እጽዋት መሀል ይገኛል። በደራሲ ሀዲስ አለማየሁ ፍቅር እስከ መቃብር ውስጥ የተጠቀሱትን መንደሮች አቀማመጥና የቤቶች አሰራር ሲመለከቱ ድንገት የዋና ገፀ ባህሪዎቹ የበዛብህና ሰብለ ወንጌል ታሪክ ትውስ ይላል። በቦታው የካህናት ዜማ እና የከበሮው ድምፅ ሲያስተጋባ በምናብ ይደመጣል። የዲማ ጊዮርጊስ ደብር ዙሪያውን የታጠረ ሲሆን ከድንጋይና ከጭቃ የተገነባ ነው። ከፍታው ሁለት ሜትር ተኩል ይደርሳል። ውፍረቱ ደግሞ ከሁለት ሜትር በላይ እንደሚሆን ይገመታል። ይህ አጥር በክረምት ወቅት አረምና የሙጃ ሳር ስለሚበቅልበት ከርቀት ሲታይ ቁጥርነቱን ለመለየት እንደሚያስቸግር የአካባቢው ነዋሪዎች ይናገራሉ። መሀል ላይከነ ግርማ ሞገሱ ጉብ ብሎ የሚታየው የጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ጣሪያ ከረጃጅም የጥድ፣ የወይራና የዋንዛ ዛፎች በላይ ከፍ ያለ ነው።

 ጣሪያው የቆርቆሮ ክዳን ሲሆን ከጣሪያው አናት ላይ ባለው ጉልላት የተንጠለጠሉት መርገፎች (በጉልላቱ እና ክፈፉ ላይ የሚሰቀሉ የቤተክርስቲያን ጌጦች) ወትሮም ቢሆን ነፋስ ሲያነቃንቃቸው ጥዑመ ዜናም ይለግሳሉ። ጉሉላቱ ላይ ደግሞ ባለ 15 ጫፍ የሆነ ከነሐስ የተሰራ መስቀል ከነግርማ ሞገሱ ይታያል። ወደ ጥንታዊው ገዳም ውስጥ ብዙም ዘልቀን ሳንገባ በስተሰሜን አቅጣጫ በግምት 50 ሜትር ሲቀረን የመነኮሳቱን የመኖሪያ ገዳም እናገኛለን። የመነኮሳቱ መኖሪያ ገዳም እንደ ግብር ማብያ አዳራሽ የተንጣለለ ነው። መነኮሳቱ የሚተዳደሩት በግብርና ነው። ንብ ማነብ፣ የፍየል ርባታ እንዲሁም ከመኖሪያቸው ጀርባ በሚገኝ ቦታ ላይ የጓሮ አትክልትና የአገዳ እህል ያመርታሉ። ራሳቸውን ከማስተዳደር ባሻገር ቤተክርስቲያኑን ይንከባከባሉ።

ዲማን አሁን አሁን የተለያዩ የአገር ውስጥ ጎብኚዎች መዳረሻቸው አድርገውታል። በተለይ ሴት የቅኔ መምህሯን ለማየት እና ቅርሶቹን ለመጎብኘት በርካታ ሰዎች ወደ ስፍራው ማምራት ጀምረዋል። የዝግጅት ክፍላችን ዘጋቢ በቦታው ተገኝቶ ይሄን መታዘብ ችሏል። የአገር ውስጥ እና የውጭ ጎብኚዎች ስፍራውን እንዲመለከቱ አስጎብኚዎች ከዚህ በተሻለ መንገድ ጥረት ማድረግ እና የማስተዋወቅ ስራ መስራት ይኖርባቸዋል። ወደ ገዳሙ ከመገባቱ በፊት በስተምዕራብ አቅጣጫ ከአጥር ውጭ ራቅ ብሎ በትናንሽ ጐጃዎቹ የተከበበ አንድ አሮጊ የቆርቆሮ ቤት ይገኛል። የዲማ ጊዮርጊስ መንፈሳዊ ትምህር ቤት ነው።

ጎጆዎቹ ዙሪያቸውን በሰንሰል ታጥረዋል። ፍቅር እስከ መቃብርን ካነበቡ ወይም ትረካውን ከሰሙ ይህን ጊዜ አንድ ነገር በአይነ ህሊናዎ ይመጣበዎታል። ይህም የፍቅር እስከ መቃብሩ የበዛብህ ቦጋለና የቅኔ መምህሩ የአለቃ ክንፈ የቅኔ ማዕበል መሆኑን ወዲያው ይረዳሉ። ከጎጆዎቹ አለፍ ብለን ወደ ቤተክርስቲያኑ ስንገባ አጥሩ በደቡብና በምእራብ አቅጣጫ ሁለት በሮች እንዳሉት እናያለን፡፡ ዋናው የምዕራቡ በር ነው። ይህ በር ደጀ ሰላም ይሰኛል። ሶስት ሜትር በሶስት ሜትር ስፋት አለው። አገልግሎቱ ለመውጫና መግቢያ ነው።ከላይ ባለ አንድ ደረጃ ህንፃ ይዟል። የፎቁ ርብራብ ከተጠረበ ጽድ ጣሪያው ደግሞ ከቆርቆሮ የተሰራ ነው።

በደጀ ሰላሙ የተገናኘ ሰው የእግዜር ሰላምታ ተለዋውጦ ማለፍ ባህሉ ነው። በቅጥሩ ውስጥ ዕድሜ ጠገብ የጽድ ዛፎችና ጥቂት መቃብር ቤቶች ይታያሉ፡፡ መቃብር ቤቶችን የደብሩ አገልጋይ የሆኑ ሴት መነኮሳትና አቅመ ደካሞች ይኖሩባቸዋል። በክብ ቅርፅ የታነፀው የዲማ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ግድግዳው ከድንጋይና ከሲሚንቶ የተዋቀረ ነው። በሶስት አቅጣጫዎች በሮች አሉት። በሮቹ ባለሰፋፊ የጽድ ሳንቃዎች ናቸው። ከመስታወትና ከብረት በመስቀል ቅርጽ የተሰሩ 30 የሚደርሱ መስኮቶች አሉት። የገዳሙ ውስጣዊ ገጽታ በተዋቡ ጥንታዊ ስዕሎች የተነቆጠቆጠ ነው። በጨርቅ ላይ የተሳሉ የቅዱሳን ስዕሎች በተጠረበ እንጨት ላይ ተወጥረው ለዕይታ ቀርበዋል።

ድንቅ ቅርሶች

ታሪካዊው ገዳም በውስጡ የተለያዩ ሃይማኖታዊ እና ባህላዊ ቅርሶችን እንዲሁም የነገስታትን አሻራ ይዟል። ከብዙ በጥቂቱም የአፄ ዮሀንስ አራተኛ የወርቅ ዘውድ፣ የወርቅ መስቀሎችን፣ የአፄ ይሳቅ የወርቅ ጫማ፣ የበትረ ሙሴ ተምሳሌት የሆነ የወርቅ ዘንግ በገዳሙ ይገኛሉ። የንጉስ ተክለሐይማኖት ጦር፣ በስዕል የተዋቡ በርካታ ጥንታዊ የብራና መጽሐፍት፣ አርባአቱ ወንጌልና ገድለ ጊዮርጊስ የተባሉ ጥንታዊ ጽሁፎች አሁንም በገዳሙ ይገኛሉ።

 አፄ ሚኒሊክ ለዲማ የሰጡት ውስጡ በህብረ ቀለማት ያማረ እና እስከ 70 ሰዎችን መያዝ የሚችል ክብ ቅርጽ ያለው ድንኳን አለ። ድንኳኑ ለክብረ በዓላት እና አስፈላጊ ለሆኑ ጊዜዎች ብቻ ይወጣል። የራስ መኮንን ካባና ሌሎች የጽሁፍ መረጃዎችን እንዲሁም የወርቅ እና የብር መገልገያዎቸ አያሌ ናቸው። ይሁንና እስካሁንም የጎብኚ ያለህ እያሉ የሚጣሩ ይመስላል። ለቅርሶቹ የሚሆን ደረጃውን የጠበቀ ሙዚየም እየተገነባ ሲሆን፤ አጠቃላይ ወጪው እስከ አራት ሚሊዮን ብር እንደሚፈጅ ካህናቱ ይገልጻሉ። አብዛኛው ስራው ተጠናቋል። በብል እና በተባይ እየተጎዱ የሚገኙ ጥንታዊ ብራና መጽሐፍትን ከጉዳት ለመከላከል አይነተኛ መፍትሔ ነው። እስካሁን ቅርሶቹ የሚገኙት በእቃ ቤት ውስጥ ነው። በዚህ ስፍራ መቀመጣቸው ለጉስቁልና የዳረጋቸው ቢሆንም በቀጣይ ጊዜያት ወደ ዘመናዊው ሙዚየም እንዲገቡ ተደርጎ ምቹ አየር እንደሚያገኙ ይጠበቃል።

የአብነት ትምህርት

በአስተዳደሩ በኩል የገዳሙን ማህበረሰብ በአራት ተከፍሎ ተመድቧል፡፡ ክፍፍሉም የሹም ሽር ቤት፣ የቄስ ቤት፣ የመሪ ቤት እና የጨዋ ቤት በመባል ተሰይሟል። የሹም ሽር ቤት የሚባለው ለደብርነት ማዕረግ ወይም በቅኔ ማህሌት እያገለገሉ ስለ ሀገር ጉዳይ ለሚቆረቆሩ የሚሰጥ ሹመት ነው፡፡ የሹም ሽር ቤት ውስጥ በወቅቱ የተሾሙትንና የተሻሩትንም ያጠቃልላል፡፡ የቄስ ቤት የሚባሉት ትምርታቸውን እየተከታተሉ ከቤተ መቅደስ በድቁና፣ በቅኔ ማህሌት፣ ሰአታት በመቆም፣ ከበሮ በመምታት መቋሚያና ጸናጽል በማቀበል ሲያገለግሉ አድገው አካለ መጠን ሲደርሱ መንኩሰው ከቤተ መቅደስ በቅዳሴ የሚያገለግሉ ናቸው፡፡ የመሪ ቤት የሚባሉት ደግሞ ከዚህ በላይ በተመለከተው መሰረት አድገው ንጉስ ነን አንፈልግም ብለው ሚስት አግብተው ቤት ሰርተው በቅኔ ማህሌት እያገለገሉ ለአገር ጉዳይ ሲወጡ ሲወርዱ የሚኖሩ መምህራን ናቸው፡፡ ሌላኛው ደግሞ የጨዋ ቤት የሚባለው ነው። ዲማ ውስጥ የተወለደ ልጅ ሁሉ በአራት ዓመቱ እንደ ደንብ ሆኖ ከቤተክርስቲያን ተማሪ ቤት ሳይገባ አይቀርም፡፡

 የጨዋ ቤት የሚባለው ግን ትምህርት ቤት ገብቶ ትምህርት እድሉ ሳይሆን ይቀርና አቋርጦ በእርሻና በንግድ የሚተዳደረውን ሰው ለመግለጽ ነው፡፡ ይህ ማህበረሰብ የጨዋ ልጅ ተብሎ እርስቱን ይዞ ቤተክርስቲያን እየደገፈ ይኖራል፡፡ ማናቸውንም የአገር ሆነ የመንደር ጉዳይ እነዚህ የማህበረሰብ ክፍሎች መክረውበት ነበር የሚፈጸመው። ህዝቡ የሚተዳደረው በመረጣቸው ልጆች ስለሆነ በየ3 ዓመቱ ምርጫ እያደረገ የሚገባው በየደረጃው እየሻሩና እየሾሙ ይኖሩ ነበር፡፡

 በዚህም የዲማ አስተዳደር አሳታፊ ነበር ማለት ይቻላል። ዲማ ለመንፈሳዊ ትምህርት ሃይማኖትን፣ ህግንና መንፈሳዊ ሥርዓቶችን ያስተምራል። በስጋዊ በኩልም መልካም አስተዳደርን፣ ሀገር ጥበቃንና እንዲሁም የወገን ፍቅርን ለህዝብ ሲያስተምር የኖረ ደብር ነው፡፡ በአብነት ትምህርት አሰጣጡ ዘመናዊ ትምህርት ባልተስፋፋበት ወቅት ጭምር እንደ አንድ ከፍተኛ ትምህርት ተቋም ከሀገሪቱ አንደኛ ጫፍ እስከ ሌላኛው ጫፍ ለሚመጡ ተማሪዎች እውቀትን ሲለግስ ኖሯል። አንጋፋው ደራሲ ዶክተር ሀዲስ አለማየሁ እና ሌሎችም ምሁራን በዚሁ የአብነት ትምህርት ቤት ተምረዋል። በዲማ የአብነት ትምህርት ቤት ውስጥ ስድስት የትምህርት ክፍሎች ይገኛሉ። እነርሱም የንባብ ቤት፣ የዜማ ቤት፣ የቅኔ ቤት፣ የቅዳሴ ቤት፣ የአቋቋም ቤትና እና የትርጓሜ ቤት በመባል ይታወቃሉ። በየትምህርት ክፍሎቹ ተማሪዎችን የሚያስተምሩ ሊቃውንት ሲገኙ ብቸኛዋ ሴት የቅኔ መምህርም ትገኛለች። የአብነት ተማሪዎች የእራሳቸው የመቃብር ቤት ውስጥ ሶስት እና አራት ሆነው ይኖራሉ።

በርካቶችም አነስተኛ ማረፊያ የምትሆን ጎጆ ቤት አሰናድተው ይኖራሉ። አሁን አሁን ከቤተሰብ ገንዘብ መደጎም ጀመሩ እንጂ የቆሎ ተማሪዎች ቀለባቸውን ለምነው ነበር የሚያገኙት። በቦታው የቅኔ ትምህርቱን የሚከታተለው ዳንኤል ይታይ ከባህርዳር ዙሪያ ለቅኔ ትምህርቱ ነው ዲማ የተገኘው። ዳንኤል እንደሚናገረው፤ በትረ ውዳሴ ማርያም፣ቅዳሴ እና መዝሙረ ዳዊትን እንዲሁም በግዕዝ ቋንቋ በሚገባ አጥንቷል። አሁን በቅኔ ቤት አንድ ዓመት ያስቆጠረ በመሆኑ እራሱን በዕውቀት ሲገመግም አጋማሽ ላይ ይገኛል። የቅኔ ቤት የጨረሰ ተማሪ ወደ አቋቋም ቤት ነው የሚሸጋገረው። በአቋቋም ቤት ደግሞ ሙሉውን ያወቀ ተማሪ ቀጣዩ ክፍል የዜማ ቤት ነው የሚሆንለት። ጠንካራ ተማሪም ከሆነ የቅኔ ቤትን ለመጨረስ እስከ ሁለት አመት ሊፈጅበት ይችላል። ነገር ግን እንደ ዘመናዊ ትምህርት ግማሹን ወይም አብዛኛውን ስላወቀ ብቻ ከአንዱ ክፍል ወደ ሌላው አይሸጋገርም። ይልቁንም ሙሉ በሙሉ ከመምህሩ የሚሰጠውን ዕውቀት ተቀብሎ ብቁ እስካልሆነ ድረስ በእድሜ ቆይታ ብቻ አያልፍም።

 ያለዕውቀት ያለፈ ተማሪ በኋላ ላይ ማነው ያስተማረህ ተብሎ ስለሚጠየቅ እና የመምህሩ ጥንካሬ ስለሚፈተሽ ሁሉም ተማሪ በቃሉ ሸምድዶ ዕውቀቱን ሲይዝ ወደ ሌላ ትምህርት ክፍል ይሸጋገራል። ግስ እና ታሪክ የመሳሰሉ መጻህፍትን ከባህር ዳር እና ከተለያዩ ከተሞች ገዝተው የሚማሩት የቆሎ ተማሪዎች በዲማ ቆይታቸው አምስትም ሆነ ስምንት ዓመት ቢቆዩ ምንም አይነት የትምህርት ክፍያ አይጠየቁም። ነገር ግን የቆይታ ጊዜ የምግብ እና የተለያዩ ወጪዎቻቸውን እራሳቸው እንዲሸፍኑ ይደረጋል። ተማሪ ዳንኤል እንደሚለው ቆሎ ተማሪ ለምኖ ካልበላ ትምህርቱ አይገባውም ተብሎ ስለሚታሰብ አንዳንድ ጊዜ በአካባቢው ከሚገኙ ነዋሪዎች ምግብ ይወስዳል። ይሁንና አብዛኛው ተማሪ ከቤተዘመድ የሚቸረውን ጥቂት ገንዘብ አብቃቅቶ በመኖር እየተማረ ይገኛል።

 በመሆኑም ቦታው የዕውቀት ማዕድ በበቁ መምህራን የሚሰጥበት በመሆኑ ዝናው ከጎጃም አልፎ በሌሎች አካባቢዎችም የናኘ ነው። ዲማ ታሪካዊነቱ በዕውቀት አበርክቶቱ ብቻ አይደለም። በጣሊያን ወረራ ወቅት የአርበኞች ማዕከል ሆኖ አገልግሏል። የመጀመሪያው የኢትዮጵያ አርበኞች ማህበር የተቆቋመበት ታሪካዊ ቦታ መሆኑንም አባ ወልደስላሴ የተባሉ የአካባቢው ታሪክ አዋቂ ይናገራሉ። በአምስት ዓመቱ የጣሊያን ወረራ ዘመንም በአባቶች ፈንታ ልጆች ተወለዱሉሽ የሚል ማህተም ተቀርፆ የጀግኖች ማህበር ተቋቁሞ አርበኞችን በተለያየ መልኩ ይረዱ እንደነበር የታሪክ ማስረጃዎች ያመለክታሉ።

የዲማ ልዩ ክስተት

በዲማ ቅዱስ ጊዮርጊስ ገዳም ብዙዎች ሊመለከቷቸው የሚጓጉላቸው መነኩሴዎች አሉ። እማሆይ ብርሐን የተባሉት መነኩሴ በቤተክርስቲያኑ ቅጥር ግቢ ውስጥ ለረጅም ዘመናት ማለትም ለ30 ዓመታት ኖረዋል። በነዚህ ሁሉ ዘመናት ግን ባዶ ሜዳ ላይ ተቀምጠው ነው ጸሎት ሲያደርሱ የሚውሉት። ነገር ግን ዝናብ ሲዘንብ እንኳን እርሳቸው የነበሩበት ቦታ ላይ ደረቅ ሆኖ ይታያል። ከብዙዎች አንደበት እንደተመሰከረላቸው መነኩሴዋ በአካባቢው ሲኖሩ የሚመገቡት ‹‹ቱልት›› የተባለው ቅጠል ነው። በጸሎት እና በምህላ አብዛኛውን ጊዜም ያሳልፋሉ። እርሳቸው ካልፈለጉ ማንም ሰው ቢመጣ ሊያናግሩ አይችሉም። አሁን ላይ ግን አነስተኛ የጭቃ ቤት በቤተክርስቲያኑ ደጀ ሰላም በስተቀኝ ተሰርቶላቸው እዛው አረፍ ይላሉ። መሬት ላይ በተቀመጡበት ፊታቸውን ወደ መሬት አድርገው በማጎንበስ ነው የሚተኙት። ለረጅም ሰዓት በዝምታ እና በጸሎት የሚያሳልፉት እናት የአካባቢው ክስተት ናቸው ቢባል ማጋነን አይሆንም። አስደናቂው የአኗኗር ዘይቤያቸው ለሩቅ አገር ሰዎችም ጭምር እንግዳ በመሆኑ አነስተኛ ማረፊያቸው ላይ መጥቶ የሚጎበኛቸው ሰው በርካታ ነው።

ተነግሮ ከማያልቀው የዲማ ጊዮርጊስ ገዳም ጥቂትም ቢሆን ጨለፍ አድርገን ወደ ናንተ ለማድረስ ሞከርን። ገዳሙ በአጠቃላይ በእጅ ያለ ወርቅ ሆነብን እንጂ በየዓመቱ በሚሊዮኖች ቱሪስቶች ሊጎበኙት የሚችሉት ድንቅ። ከአዲስ አበባ እንብዛም የማይርቀውን ይህን ታሪካዊ ቦታ መጎብኘት የሚሰጠው የመንፈስ እርካታን በሌላ በምንም መተካት አይቻልም። በተለይ የአገር ውስጥ ጎብኚዎች በዚህ ስፍራ ቢገኙ ብዙ እንደሚያተርፉ መገመቱ ብዙም ከባድ አይሆንም። ቸር እንሰንብት!!

አዲስ ዘመን የካቲት 24/2011

በጌትነት ተስፋማርያም


https://www.addisadmassnews.com/index.php?option=com_k2&view=item&id=16159:%E1%8A%A0%E1%88%B5%E1%8C%88%E1%88%AB%E1%88%9A%E1%8B%8D-%E1%8B%A8%E1%89%B0%E1%8D%88%E1%8C%A5%E1%88%AE-%E1%8B%8B%E1%88%BB&Itemid=209


ደብረ ድማሕ ዲማ ጊዮርጊስ ገዳም

ደብረ ድማሕ ዲማ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያ

የነባር ተቋማት እሴት፣ የዲማ ጊዮርጊስ ገዳም ተምሳሌትነት

ደብረ ድማሕ ዲማ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት በምስራቅ ጎጃም ዞን እነማይ ወረዳ ይገኛል። እነማይ ከአዲስ አበባ በ265 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል። ዲማ ከአዲስ አበባ በደጀን ታጥፎ ወደ ሞጣ በሚጓዘው መንገድ ከብቸና ከተማ በስተ ምስራቅ ይገኛል። ከባህርዳር ደግሞ በ222 ኪሎ ሜትር ርቀት አለው።

መግቢያ

የዚህች ጽሑፍ ዋና ዓላማ የዘመናችን ዐቢይ ጉዳዮችን በአግባቡ ለማስተናገድ እንዲቻል ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ የነባር ተግባራትን ተሞክሮ ለአንባቢያን ማቅረብ ነው። እንደምሳሌነት የተወሰደው ደግሞ የዲማ ጊዮርጊስ ገዳም አስተዳደር እና በገዳሙ የነበረው የትምህርት ይዘት ነው። የዲማ ጊዮርጊስ አንዱ ስያሜ ደብረ ድማሕ ነው። ስለሆነም ገዳሙ ዲማ ጊዮርጊስ ወይም ደብረ ድማሕ በመባል ይታወቃል። ተመሳሳይ ሁኔታዎች በሌሎች አከባቢዎች እንደነበሩ/ እንዳሉ እገምታለሁ። ነገር ግን በቂ መረጃ ማግኘት የቻልኩት ስለ ዲማ ጊዮርጊስ ብቻ ነው። መረጃዎችንም ያበረከቱልኝ የዲማ ካህናት ተወላጆች ናቸው። በተለይም ሰፋ ያለ የጽሑፍ መረጃ የተገኘው ከቄስ ዋለልኝ ትዕዛዙ መሆኑን መግለጽ እፈልጋለሁ።

የዲማ ጊዮርጊስ ታሪክ

በታሪክ (አፈ ታሪክ እና በጽሑፍ) እንደሚወሳው በአፄ አምደ ጺዮን ዘመነ መንግሥት (1297-1327 ዓም)፣ ስመ መንግሥቱ ገብረ መስቀል፣ የደብረ ድማሕ ቤተ ክርስቲያን አሁን ባለበት ቦታ ተመሠረተ። በአፄ ዳዊት (ቀዳማዊ ዳዊት) ዘመነ መንግሥት (1382-1411 ዓ.ም) ቤተ ክርስቲያኑ በሥርዓተ ገዳም ተቋቋመ። ከአፄ ይስሐቅ ዘመነ መንግሥት (1414-1429) ጀምሮ እስከ ፯ኛው መምህር እስከ አቡነ ተክለ አልፋ ድረስ መነኵሳቱ በአንድነት (ከህዝብ ተነጥለው/ ርቀው) በገዳም ሥርዓት፣ የአካባቢው ሕዝብም እንዲሁ በአንድ ወገን (ከመነኵሳቱ ተለይቶ) ይኖሩ ነበር። አቡነ ተክለ አልፋ የዲማ አካባቢ ሃይማኖታዊ መሪ የነበሩት በአህመድ ኢብን ኢብራሂም (በተለምዶ ግራኝ ተብሎ በሚጠራው) መሪ ዘመን (በ16ኛው ክፍለ ዘመን) ነበር። በዚያን ዘመን በሊቃውንት ብዛት እና ጥራት በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መንበርነት እንዲሁም በእውነተኛ መነኵሳት መኖሪያነት በዓይነቱ ስመጥር ሆኖ ነበር።

በአህመድ ኢብን ኢብራሂም የጦርነት ዘመን፣ አቡነ ተክለ አልፋ ታቦቱንና መነኵሳቱን ይዘው ተሰደዱ። የጦርነቱ ዘመን አልፎ ከስደት ሲመለሱ፣ መነኵሳቱ በፈቃዳቸው ስደት አማቶናልና (አንገላቶናልና) ከሕዝብ ተነጥሎ የብቻ (መነኮሳቱ ብቻ በአንድነት) ሰብሰብ ብሎ መኖር ይቅር ብለው አቡኑን ለመኗቸው። አቡነ ተክለ አልፋም የመነኮሳቱን ልመና ተቀብለው፣ የመነኮሳቱን ከሕዝብ ተነጥሎ መኖር አስቀርተው፣ከዓለማውያን ጋር በአንድ አካባቢ እንዲኖሩ ፈቀዱ።

አቡነ ተክለ አልፋ የአካባቢውን መሬት፣ ለማኅበር ቤት የተወሰነ ርስት አስቀርተው፣ ለመነኮሳቱና በስደት ጊዜ ጥገኝነት ሰጥተዋቸው ለነበሩ መሳፍንት (እነ ራስ ወይናጎን፣ እነ ራስ እንደበሉን እና ሌሎችንም) በርሥተኝነት መደቡ። ከዚያን ጊዜ ጀምሮ “ማኅበር” የሚባሉት ቡድን መሰል ስብስቦች፣ በተከሥተ ብርሃን ዘመን ከነበሩት ባለርስቶች እና በተክለ አልፋ ዘመን ከተሠሩት አባቶች የተወለዱት ናቸው።

አቡነ ተክለ አልፋ የመነኮሳትን ከሕዝብ ተነጥሎ መኖርን ቢያስቀሩም፣ ማህበረሰቡ ቀደም ሲል ይተዳደርበት የነበረው ደንብ ቀጥሎ ነበር። በአሰፋፈርም ቢሆን፣ ምንም ብዙ መነኮሳት ደልዳላ ቦታ ላይ ከሚገኘው ቤተ ክርስቲያኑ አካባቢ ቢኖሩም፣ ጥቂት መነኮሳት ገድ ገደል ውስጥ ከማኅበረሰቡ ተለይተው ነበር የሚኖሩት።

ለዲማ ጊዮርጊስ ገዳም የገቢ ምንጭ እንዲሆኑ፣ በተለያዩ አካባቢዎች ያሉ ቦታዎች (ክፈፎች) በአካባቢው የነበሩ መሳፍንት ከግዛቶቻቸውእየቆረሱ ለገዳሙ ገፀ በረከት ያበረክቱ ነበር።ስለሆነም በዲማ ገዳም ስር የሚተዳደሩት ክፈፎች፣ ከገዳሙ አካባቢ ከሚገኙት በቀር፣ ሌሎች ኩታ ገጠሞች አይደሉም። ለምሳሌ ደብረ ማርቆስ አከባቢ፣ ከገዳሙ ከስድሳ ኪሎሜትር ርቀት በላይ የሚገኙ፣ በገዳሙ የሚተዳደሩ ክፈፎች አሉት። በገዳሙ አስተዳደር ስር ያሉ ክፈፎች የሚተዳደሩትም ዲማ ገዳም በሚሰይምላቸው ጭቃ ሹሞች ነበር።

የኢትዮጵያ ነገሥታት ደግሞ ለገዳሙ ልዩ ልዩ ስጦታዎችን ያበረክቱ ነበር። ቀደም ሲል የነበሩትን እንተዋቸውና በቅርብ ዘመን አፄ ቴዎድሮስ የወርቅ መቋሚያ እና የወርቅና የብር መስቀሎች፤ አፄ ዮሐንስ ደግሞ የወርቅ የራሥ ቁር እና የወርቅ ጫም ለዲማ ገዳም አበርክተዋል (ስጦታው/ በረከቱ ንስሃ መሰል ገፅታ የተላበሰ ነበር)።

የዲማ ማኅበረሰብ ይተዳደርበት የነበረው ሥርዓት

የዲማ አካባቢ ማኅበረሰብ (ማኅበሩ) በአራት ክፍል የተመደበ ነበር። አንደኛ “የሹም ሽር ቤት”፡ ሁለተኛ “የቄስ ቤት”፣ ሦስተኛ “የመሪ ቤት” እና አራተኛ “የጨዋ ቤት” የተባሉት ነበሩ።ራሳቸው ከመሾም እንዲሁም ሹሞችን ከመምረጥ፣ በጠቅላላው በሀገር አስተዳደር የማይሳተፉ፣ በጸሎት፣ በፍታት፣ በተስካር በአትርሱኝ ብቻ የሚኖሩ፣ “የሰዓታት ቤት”፣ “የገዳማት ቤት” የሚባሉ ሁለት ክፍል ማኅበሮችም ነበሩ። የዚህ ስብስብ አበላት ከላይ እንደተጠቀሰው፣ አይመርጡምም፣ አይመረጡምም። የማኅበረሰቡ ቤት ብሎ የመደባቸው ስብስቦች ከላይ ከተጠቀሱት ርስት የተሰጣቸው ባለውለታዎች ተወላጆች እና ነባር ባለ ርስቶች ተወላጆች ብቻ ነበሩ።

በዘመኑ የነበረው የትምህርት ይዘት

በዚያን ዘመን ዲማ የተወለደ ወንድ ልጅ ሁሉ ለትምህርት ሲደርስ (በአራት ዓመቱ) ተማሪ ቤት እንዲገባ ይደረግ ነበር። ትምህርት ዕድላቸው የሆኑት ሕፃናት ከንባብ ቤት ገብተው ዳዊት ደግመው የንባብ ትምርትን ሲያጠናቅቁ፣ የንባብ መምህሩ ወስዶ ለዜማው መምህር ያስረክባቸዋል። በዚህ ጊዜ “ሰላም ለኪ” ብለው የዜማን ትምህርት ከጀመሩበት ቀን ጀምሮ እንደ ቅድምያ እንደ ቅድምያቸው (በቅደም ተከተል) የቤተክርስቲያን አቋቋምና የተዝካር አቀማመጥ ደረጃ ይይዛሉ።

የዜማ ትምህርታቸውን ሲጨርሱ የዜማው መምህር ለቅኔው መምህር ያስረክባቸዋል። ከዚያም ቅኔ ዜማ እየተማሩ ከቤተ መቅደስ በዲቁና፣ ከቅኔ ማኅሌት ስብሐተ ነግህ ማኅሌትም እየቆሙ፣ ከበሮ በመምታት፣ መቋሚያ ጸናጽል በማቀበል ሲያገለግሉ ያድጋሉ። አካለ መጠን ሲደርሱ ምንኵስናን የመረጡ መንኵሰው በቤተ መቅደስ ያገለግላሉ። ከላይ በተጠቀሰው ሂደት አድገው ከዚያው ተምረው ከሚመነኩሱት በቀር፣ ተወላጅ ያልሆነ ከውጭ የመጣ ቄስም፣ ዲያቆንም ቢሆን፣ ከቤተመቅደስ እንዳይገባ ሥርዓቱ አጥብቆ ይከለክል ነበር። “የቄስ ቤት” የሚባለው የማኅበረ ሰቡ አካል የነኝህ መነኵሳት ስብስብ (ክፍል) ነው።

ሁለተኛው ክፍል፣ ምንኵስናን አንፈቅድም ብለው፣ ሚስት አግብተው ቤት ሠርተው በቅኔ ማኅሌት እያገለገሉ፣ በሀገር ጉዳይ ሲወጡ ሲወርዱ የሚኖሩ መዘምራን “መሪዎች” ይባላሉ። የእነዚህ የደብተሮች አንድነት (ስብስብ) ነው “የመሪ ቤት” የሚባለው።

ሦስተኛው “የሹም ሽር ቤት” የሚባለው በደብተርነት ማዕረግ፣ በቅኔ ማኅሌት እያገለገሉ ቆይተው፣ “በዘጠኝ ባለወግ” ተመርጠው፣ “ገበዝ”፣ “መጋቢ”፣ “እራቅማሰራ”፣ “መሪጌታ” ተብለው የተሾሙ እና የሹመት ጊዜያቸውን ጨርሰው ሹም መሆናቸው ያከተመ መዘምራን አንድነት (ስብስብ) ነው።

አራተኛው “የጨዋ ቤት” የተባለው በአራት ዓመቱ ከተማሪ ቤት ከገባ በኋላ፣ ትምህርት ዕድሉ ሳይሆን ቀርቶ፣ በእርሻና በንግድ የሚተዳደር ሲሆን፣ የጨዋ ልጅ ተብሎ ርስቱን ይዞ ቤተ ክርስቲያንን በጉልበት፣ በገንዘብ፣ እየደገፈ ይኖራል። የገዳሙን ሹሞች የመሾም የመሻር ሥልጣን ያላቸው “ዘጠኙ ባለወጎች” የሚመረጡት ከእነዚህ በአራት ክፍል ከተመደቡት ባለ ርስቶች (ተወላጆች) ነው።

የ«ዘጠኙ ባለወጎች» አመራረጥ

የ”ዘጠኙ ባለወጎች” ስብስብ ማኅበረሰቡ በውክልና የገዳሙን አስተዳዳሪዎች የመሻር/ የመሾም ሥልጣን የተሰጣቸው የማኅበረሰቡ አባላት (ስብስብ) ናቸው። ሹም ሽር በሚደረግበት ጊዜ በቧኝ ተለፍፎ (በስማ በለው)፣ እነዚህ በአራት ክፍል የተመደቡት ባላባቶች ተሰብስበው፣ በአንድነት ይመክራሉ። ከዚያ በኋላ ሹመት ይገባናል የሚሉ መዘምራን ከሹም ሽር ቤትና ከመሪ ቤት እየተነሡ፣ አገልግሎታቸውን እያስረዱ፣ ለአባቶቻችን ማዕረግ አብቁን እያሉ ልመናቸውን ያቀርባሉ።

ከዚያም የአራቱ ክፍል ማኅበር (ስብስብ)፣ ለየራሳቸው ተለይተው ይመክራሉ። “የሹም ሽር” ቤት ብቻውን መክሮ የታመኑ ሦስት፣ “የቄስ ቤትም” እንደዚሁ በበኩሉ ታማኝነት ያላቸው ሁለት፣ “የመሪ ቤትም” እንዲሁ የሹመት ፈቃድ የሌለባቸውን (ለመሾም የማይፈልጉ) ሁለት፣ “የጨዋ ቤትም” ደግሞ ሁለት ሽማግሎችን መርጠው ያቀርባሉ። በጠቅላላው ዘጠኝ ምርጦች ይገኛሉ፣ እነኝህ ግልሰቦች ናቸው “ዘጠኙ ባለወጎች” የሚባሉት። የተለያዩ ክፍሎች መራጮቹን የመወከል ስልጣን ይለያያል። “የሹም ሽር” ቤት ሦስት ተወካዮች ሲመርጥ፣ የተቀሩት ሌሎች ክፍሎች ሁለት፣ ሁለት ወኪሎች ብቻ ነው የሚመርጡ። ይህም ቀደም ሲል ሹሞች የነበሩ ስለ ገዳሙ አስተዳደር የበለጠ ግንዛቤ ይኖራቸዋል ከሚል እይታ የመነጨ ይመስላል። “ዘጠኙ ባለወጎች” እንደተሰየሙ፣ ወዲያው ሥዕል መስቀል ቀርቦ፣ ለወዳጅ ለዘመድ ብለን አናዳላም። ለሀገር የሚጠቅመውን በእውነት እንመርጣለን እያሉ ይምላሉ። የሚመረጡት ሹሞች አንደኛ የገዳሙ መምህር (ከሁሉም ሹሞች በላይ ሆኖ የሚሰየመው)፣ ሌሎች ገበዝ፣ መጋቢ እና እራቅማሰራ ናቸው።

የገዳሙ ሹሞች አመራረጥ

መምህሩ በመላ ማኅበር ፈቃድ በትምህርቱ፣ በትሩፋቱና በግብረ ገብነቱ ተመርጦ ይሾማል። ማኅበሩ ባልተስማሙበት ጊዜ በድምፅ ብልጫ ይሾማሉ እንጅ እንደ ሌሎች ሹማምንት በምረጡኝ ሂደት አይሾሙም። የተሾመው መምህር ጉባኤ ሠርቶ ለማስተማር የሚችል ከሆነ፣ በሱባዔ ተወስኖ፣ በማስተማር ጸንቶ ይኖራል። ጉባኤ ሠርቶ ለማስተማር የማይችል ከሆነ፣ እግሩ ከመቆም፣ አንደበቱ በጸሎት ከመደመም ሳይለይ፣ በመዓልትም በሌሊትም ቤተ እግዚአብሔር በማገልገል ይኖራል። ስለሀገር አስተዳደር ገበዙንና መጋቢውን እራቅማሰራውን ተከትሎ የሚሠራ፣ “ተቋጣሪ” (ወኪል) የወደደውን ከመዘምራኑ መርጦ መምህሩ ይሾማል። በማናቸውም ጉዳይ መምህሩ አይወጣም፣አይወርድም። መምህሩ ነውር ቢገኝበት፣ ከማኅበር አልስማማም ቢል በደንቡ መሠረት በማኅበር ተመክሮ ይሻራል። ከተሻረም በኋላ በማናቸውም ምክንያት ችግርና ውርደት እንዳያገኘው፣ የማኅበር ቤት ከሚባሉት አገሮች (ክፈፎች) አንዱ፣ በማኅበር ተመክሮና ተመርጦ በሕይወት እስካለ ድረስ መተዳደሪያ ይሰጠዋል።

“ገበዙ” የሚመረጠው ከዚያ በፊት፣ ቀደም ሲል በመጋቢነት ወይም እራቅማስራነት ተሹመው ከነበሩ፣ ከሹም ሽር ቤት ነው። መጋቢውና እራቅማሰራው ግን ከቤተ እግዚአብሔር በማገልገል ስለሀገር ጉዳይ በመላክ፣ ሲወጡ ሲወርዱ ከቆዩት፣ “ከመሪ ቤት” ይመረጣሉ። ሹም ሽር የሚደረገው በየሦስት ዓመቱ ነው። ሆኖም ግን ቀደም ሲል ከተመረጡት መካከል ለሀገር ጠቃሚነታቸው ከታመነበት ከሦስት ዓመት በላይ የሹመት ዘመን የሚጨመርለት ሹም ቢኖር ደምቡ አይከለክልም።

የ«ዘጠኙ ባለወጎች» የውክልና ተግባር

መምህሩ የሚመረጠው በዘጠኙ ባለወጎች ሳይሆን በአጠቃላይ በማኅበረሰቡ ነው። ዘጠኙ ባለወጎች ወዲያው እንደተሰየሙ፣ሳይውል ሳያድር ሕዝቡ ተቀምጦ ስለሚጠብቃቸው የሦስቱን የገዳም ሹሞች ምርጫ ያካሂዳሉ። የዘጠኙ ባለወጎች ስብስብ “ገበዝ”፣ “መጋቢ” እና “እራቅማሰራ” ይመርጣል። የአመራረጡ ሥነ ሥርዓትም መስፈርት አለው። መስፈርቶቹ በአራት ምድብ የተከፈሉ ናቸው፡- አንደኛው፣ ተምሯል፣ በጉባኤ ውሏል፣ ምሥጢር አደላድሏል፣ ወልድ ዋህድ የምትል ሃይማኖታችንን ይጠብቅልናል፣ ብንጠይቀው ይመልስልናል (ያስረዳናል)፤ ሁለተኛው፣ አንደበት አለው (አንደበተ ርትኡ ነው)፣ ከአደባባይ ይውላል፣ ነገር ያውቃል፣ ከቡታ (ከሃብታም)ና ከመስለኔ ተከራክሮ ቅፈፋችንን/ የአስተዳደር ግዛታችንን) ይጠብቅልናል፣ ደብራችንን ያስከብርልናል፤ ሦስተኛው፣ ሃብት አለው፣ እንጀራ አለው፣ እንግዳ ቢመጣ ይቀበላል፤ አራተኛው፣ ስለሀገር ጉዳይ በመላላክ፣ ወጥቶ ወርዶ ሀገሩን አገልግሏል የሚሉ ታሳቢዎችን ከግምት ውስጥ የሚያስገቡ ናቸው። በዚህም በስም፣ በቦታ ይክበር ብለው ፈርደው፣ ቢስማሙ በአንድ ድምፅ፣ ባይስማሙ በድምፅ ብልጫ ግብዝናውን ለእገሌ፣ መጋቢነቱን እና እራቅማሰራቱን ለእገሌ ሰጥተናል ብለው ይወስናሉ። ከዚያም በስምምነት የደረሱበትን ውሳኔለተሰበሰበው ሕዝብ ያሳውቃሉ።

ህዝቡም ቅሬታ ሳይሰማው የተመረጡትን ሹሞች በደስታ ይቀበላል። ከዚያም ማኅበረሰቡ የተመረጡትን ለሹመታቸው እውቅና ሰጥቶ፣ እንደየማዕረጋቸው ያከብራቸዋል፣ ይታዘዛቸዋልም። ሹሞች ከተሰየሙ በኋላ፣ በዚያኑ ሰሞን የማኅበረሰቡ አባላት (የአካባቢው ሕዝብ) በሙሉ አንድ በአንድ በመሶብ እንጀራ በገንቦ ጠላ እጅ መንሻ ለሹሞች ያገባል።

የ«መሪጌታው» ሹመት

መሪጌታነቱን የሚሾመው አመልጥኖ መርቶ፣ አመርግዶ ጸፍቶ፣ ቅኒ ቢጎድል ሞልቶ፣ መውጣት የሚቻለው ባለሙያ ካህን ተመርጦ ነው። ተመራጮቹም ሆኑ መራጮቹ “የመሪ ቤት” በሚባለው ማኅበር (ከአራቱ አንዱ ክፍል ብቻ) የሚገኙት መዘምራን ናቸው። እነሱም መሪጌታውን መርጠው፣ ሹመው፣ አልብሰው አስጠምጥመው፣ ወስደው፣ ከመምህሩ ጀምረው በሹመት ለከበሩት ሹሞች ለሚባሉት እጅ ያስነሳሉ። ሹሞቹም ደግሰው ይቀበሏቸዋል።

የመሪጌታው መብትና የሥራ ክፍል

የማኅበሩ አባላት በሰላም ለኪ (ጠቅለል ብሎ ሲታይ በዕውቀት) እኔ እበልጣለሁ፣ እኔ እበልጣለሁ በመባባል ቢካሰሱ፣ ዳኛ ሆኖ የሚሰየመው መሪጌታው ነው። ተዝካር ቢደግስ፣ እንደዬ ማዕረጋቸው፣ በሥርዓት አስቀምጦ የሚጋብዝ መሪጌታው ነው። የአትርሱኝ ወይም የፍታት ገንዘብ ቢገኝም፣ የመሪ ቤቶችን ድርሻ ተካፍሎ በደንብ በሥርዓት የሚያካፍል መሪጌታቸው ነው። በቤተክርስቲያን አገልግሎትም በቅኔ ማኅሌት የሚያገለግሉትን “የሹም ሽር” እና “የመሪ ቤቶችን” በየተራቸው የሚያዛቸው መሪጌታው ነው። ትእዛዝ ሲሰጥም የመሪ ቤቱን አባል አዋቂነት፣ የበዓሉን ታላቅነት እያመዛዘነ ያዛል እንጅ፣ በሙያ አነስተኛ የሆነውን ሰው በአበይት በዓላት ጊዜ ለዚህ ተግባር አያሰማራም።

የ«ሊቀ አበው» ሹመት እና ሥልጣን

“ሊቀ አበው” ከመዘምራኑ በገበዙ ተመርጦ ይሾማል። ሊቀ አበውም በውስጡ የሚታዘዙ የሥራ ረዳቶች፣ ሁለት ጓደኞች፣ ከጨዋ ቤት ይሾማል። በሀገር ላይ የሚመጣውን ችግር ለመፍታት የሚያገለግል ማናቸውንም ትእዛዝ ከገበዙ እየተቀበለ (ሁለቱ ጓደኞች እየረዱት) ትዕዛዝ የሚያስፈጽም ሊቀ አበው ነው።

በአራቱ ዋና የገዳሙ ሹሞች (በመምህሩ፣ በገበዙ፣ በመጋቢ እና በእራቅማሰራው) መካከል ቅራኔ ተከስቶ የአንደኛቸው ወይም የሁሉም ሹሞች ስልጣን በሌሎች ተይዞ እንዲቆይ ቢያስፈልግ፣ የሁሉንም ሹሞች ስልጣን ይዞ የሚቆይ (የሚይዝ) “ሊቀ አበው” ነው።

የሹሞች የዳኝነት/ የአስተዳደር ሥርዓት

በማናቸውም ጉዳይ/ችግር ገበዙ፣ መጋቢው እና እራቅማሰራው ችግሩ የተነሣበትን አከባቢ ጭቃ ሹም እንደ ቋሚ ዳኛ አድርገው ይመለከቱታል። ጭቃ ሹሙ ነው በቅርብ ለማኅበረሰቡ ችግር ፈች የሚሆነው። ጉዳዩ ከጭቃ ሹሙ ሥልጣን በላይ ከሆነ (የጭቃ ሹሙ ስልጣን በደምብ የተወሰነ ነው)፣ ሹሞቹ (ገበዙ፣ መጋቢው እና እራቅማሰራው) ጉዳዩን ራሳቸው ከመረመሩት በኋላ፣ መምህሩ የማያስፈልግ ቀለል ያለ ጉዳይ ከሆነ እዚያው ይቋጩታል። ጉዳዩ ከበድ ያለ ከሆነ ግን መምህሩ ባሉበት ለፍርድ ዓርብና ረቡዕ ይቀጠራል።

አራቱም ሹማምንት በሚገኙበት ጉባዔ ጉዳዩ ተመርምሮ ከተጣራ በኋላ፣ ቢስማሙ በአንድ ድምፅ፣ ባይስማሙ በድምፅ ብልጫ ጉዳዩ ይወሰናል። ከዚያ ግራ ቀኙ ተከራካሪዎች ቀርበው፣ የተሰጠው ፍርድ “በጎጃም ነጋሹ” ይነገራቸዋል። የዳኝነቱንም ገንዘብ መምህሩ፣ ገበዙ፣ መጋቢው እና እራቅማሰራው አራቱ እኩል ይካፈሉታል። የገበያውንም ቀረጥ በጭቃ ሹሙ፣ በሊቀ አበውና በጓደኞቹ አስቀርጦ ለአራቱ ሹማምንቶች ገቢ ያደርጋል።

ስለቤተክርስቲያን አቋቋም በቀኝም በግራም ቢሆን ከመምህሩ ቀጥሎ ገበዙ፣ ከገበዙ ቀጥሎ መጋቢው፣ ከመጋቢው ቀጥሎ እራቅማሰራው ይቆማሉ። በመሪ ቤት ያሉ ደብተሮችም በሹማምንት ካልከበሩ በቀር ከመሪጌቶች ቀጥለው በየሰላም ለኪአቸው (በተመደበላቸው ቦታ) ይቆማሉ። ከመሪ ቤት ማኅበር ያልገቡ፣ በተማሪ ቤት ያሉ ወጣቶችም እንዲሁ በየሰላም ለኪአቸው ይቆማሉ። በተዝካርና በምሳ ጊዜም አቀማመጣቸውም እንደዚሁ እንደ አቋቋማቸው ነው።

የመምህሩ ወኪል (ተቋጣሪ)

የመምህሩ ወኪል (ተቋጣሪ) በመምህሩ ፈቃድ ከመዘምራኑ መካከል ተመርጦ ይሾማል። በተለይ ለመምህሩ መተዳደሪያ የሆኑትን አገሮች፣ ስለመምህሩ ሆኖ ያስተዳድራል። እነዚህ አገሮች ለመምህሩ የሚያስገቡትን ግብር ያስገባል። በሌሎችም ክፈፎች ከገበዙ፣ ከመጋቢው እና ከእራቅማሰራው ጋር ሆኖ ይሠራል። ይሁን እንጂ የሹሞች የበላይነት መብት የለውም።

የ «ጎጃም ነጋሽ» ሹመትና መብት

“ጐጃም ነጋሽ” የሚባለው ጭቃ ሹም ነው። ጭቃ ሹሙ የጨዋ ቤት ከሚባለው ማኅበር ክፍል በጨዋ አንድነት (ስብስብ) ተመርጦ፣ በአራቱ ሹማምንት ፈቃድ ይሾማል። የደብሩንም ሕዝብ እንደ ደንቡ በጭቃነቱ ያስተዳድራል። ከደብሩ የሚገኘውን የገበያ ቀረጥ፣ የዳኝነት ገንዘብ እንደ ዋስ አጋች ሆኖ እየሰበሰበ ለአራቱ ሹማምንት የሚያካፍል እሱ ነው።

ስለ «ቤተ አበዎች»

ዲማ በአቡነ ተክለ አልፋ ጊዜ፣ የአንድነት ገዳምነቱ ቀርቶ ርስቱ ለማኅበር የተወሰነ ተመድቦ ባለርስት ሲመራበት፣ የቀረው መሬት ለዘጠና አበዎች ተከፍሎ ተመድቧል (ዘጠና አበዎች ባለ ርዕስት ሆነውበታል)። እነዚህ ዘጠና አበዎችም በአሥራ ስምንት፣ በአሥራ ስምንት ተከፍለው ለአምስት ዐቢይ ክፍሎች ተመድበዋል። ይህ ምድብ እንዳይፋለስ፣ ድንበር እንዳይጣስ፣ የአበዎች ስም እንዳይደመሰስ፣ የሚጠብቁ የርስት ዳኞች፣ አምስት ቤተ አበዎች ተሾመዋል። እኒህም “ዕቃ ቤት”፣ “ግራ ቤት”፣ “ተርቢኖስ”፣ “ተንሥኤ መድኅን” እና “ቤተ ዮሐኒ” ይባላሉ። ይህን ሹመት እኒህ ሰዎች በጊዜው ተገኝተው ስለተሾሙ በእነርሱ ስም ይጠራል እንጂ፣ በዘር እየወረደ የእነርሱ ዘር ብቻ የሚሾምበት ሥርዓት አይደለም። በአምስት ዐቢይ ክፍሎች ከተከፈሉት፣ በአሥራ ስምንት መደብ ከተመደቡት አበዎች የተወለዱት ሁሉ እንደየክፍላቸው በየቤት፣ በየቤቱ ይሾማሉ።

በደብረ ድማሕ ጊዮርጊስ (በዲማ ጊዮርጊስ ገዳም) የነበረውን የሹሞች አሰያየም እና የተግባር ድርሻ ሲፈተሽ፣ የሹሞች አሰያየም በማህበሩ ምርጫ/ ፍላጎት ላይ የተመሠረተ፣ ብሎም ጠቅለል ብሎ ሲፈተሸ ዴሞከራሲያዊ እንደነበረ ያመለክታል። የሹሞችም ተግባር መሬት የነካ፣ ችግር ተኮር እና ችግር ፈች እንደነበረ ያሳያል። ምናልባትም ከእንደዚህ ዓይነት የአስተዳደር  ሥርዓት ልንወርሰው የምንችለው አካሄድ ይኖር ይሆን? የሚል ጥያቄ አስነስቶብኛል። ለጥያቄውም አዎንታዊ እይታ አለኝ። ነባር ሥርዓትን ከዘመናዊ ሂደት ጋር ማዛመጃ፣ ማገናኛ ድልድይ ማድረግ ይቻላል በሚል።

ትምህርት በዲማ ጊዮርጊስ/በደብረ ድማሕ/

በደብረ ድማሕ ገዳም፣ በነበረው የትምህርት ሥርዓት፣ እንደ ዘመናችን የዩኒቨርሲቲ ትምህርት ክፍሎች መታየት የሚችሉ፣ የተለያዩ የትምህርት ክፍሎች ነበሩ። እነሱም፡- የ“ጸዋተወ ዜማ” (ልዩ ልዩ ዜማዎች እና መዝሙሮች) ትምህርት፣ የ“ግዕዝ ቋንቋና ቅኔ ትምህርት”፤ የ“ሃይማኖት ትምህርት” (የሥነ መለኮት ትምህርት)፣ የ“ብሉያት ትርጓሜ ትምህርት”፤ የ“ሐዲሳን ትርጓሜ ትምህርት”፣ የ”ሊቃውንት መጽሐፍት ትርጓሜ ትምህርት” እና የ“መጻሕፈተ መነኮሳት ትርጓሜ ትምህርት” ነበሩ። በመሆኑም ደብረ ድማሕ ከላይ ለተጠቀሱት የትምህርት ዓይነቶች ማዕከል ሆኖ ለዘመናት ቆይቷል።

ዲማ በልብወለድ መልክ ቢሆንም (በፍቅር እስከመቃብር)፣ በሀዲስ ዓለማየሁ በሰፊው እንዲታወቅ ተደርጓል። የደብረ ድማሕ የትምህርት ማዕከልነት፣ ታዋቂነት ከ19ኛው ምእተ ዓመት ጀምሮ እየመነመነ ቢመጣም፣ እርሾው ግን እስከዛሬ ድረስ አልጠፋም።

ዲማ ስለነበረው ትምህርት (በተለይ ቅኔ)፣ ጠቀም ያለ መረጃ ከመጽሐፈ ትዝታ (ዘ አለቃ ለማ ኃይሉ ወልደ ታሪክ፣ ደማሙ ብዕረኛ መንግሥቱ ለማ እንደጻፈው) ማግኘት ይቻላል። በአሥራ ዘጠነኛው ምዕተ ዓመት አጋማሽ፣ አለቃ ለማ ኃይሉ ዲማ ጊዮርጊስ የቅኔ ተማሪ ነበሩ። እሳቸውም ስለ ዲማ ሊቃውንት በሰፊው በትዝታቸው አስፍረውታል። የአለቃ ለማ ኃይሉ መምህር አለቃ ተጠምቆ በፈንጣጣ ምክንያት በሕጻንነታቸው ማየት የተሳናቸው ነበሩ። የመምህሩ እናት ትውልድ አገር አባ ገሪማ (አድዋ አጠገብ)፣ አባታቸው ደግሞ የሽሬ ተወላጅ ነበሩ። የቅኔ መምህር ሆነው ነበር ካገራቸው ከትግራይ የወጡ። ዕውቀታቸውን ያለጊዜ ገደብ ለማዳበር ግን መጀመሪያ ስሜን (ጐንደር)፣ ከዚያ ወደ ጐጃም ተሻግሩ። ዋሸራ የቅኔ ጉባዔ ዘርግተው ሳለ፣ ወደ ሞጣ ሄደው፣ አገር ባደነቀው ፍጥነት (በሦስት ዓመት) የብሉይ ሊቅ (ጠበብት) ለመሆን በቅተዋል። ከዚያም ወደ ዲማ ዘልቀው የቅኔ መምህር፣ ብሎም የብሉይ መምህር ሆኑ – ጣምራ ፕሮፌሰርነት።

አለቃ ለማ ኃይሉ እንዳሉት፣ አለቃ ተጠምቆ ዲማ የተቀመጡበት ዋና ምክንያት፣ መጽሐፍ እንደልብ ይገኝ ስለነበር (ግለሰብ ሊገዛው የማይችል ብዙ መጽሐፍ ዲማ ተከማችቶ ስለነበር) ነው ይላሉ። ይህም እገረ መንገዱን፣ በዚያን ጊዜ መጽሐፍት ከፍተኛ ዋጋ እንደነበራቸው ያመለክታል። ይህም በቅርብ ጊዜ ለተመሠረተው ስለ “አብርሆት መጻሕፍት ቤት” አስፈላጊነት አንድ ተጨባጭ ምስክር ሊሆን እንደሚችል ልብ ሊባል ይገባል።

በአገር ውስጥ ሁሉ ቅኔ ሲዘራ ይውላል ይባል በነበረበት በዚያን ወቅት፣ የሰቆጣው ተወላጅ አለቃ ሠረገላ ብርሃን ዲማ ነበሩ። መሪጌታ ውብሸት (ስመ ጥሩው የብቸና ተወላጅ የቅኔ ሊቅ)፣ እንዲሁም የአድዋው ተወላጅ አለቃ ትኩ እና የላስታው ተወላጅ ደቂቁ አለቃ ለማም የዲማ ሊቃውንት ስብስብ አካል ነበሩ። ሁሉንም ሊቃውንት ዲማ ላይ ያሰባሰባቸው ድምበር ዘለል የዕውቀት ፍላጐት እንደነበር ይነገራል። ሊቃውንቱ በዘመኑ በተከሰተው ቸነፈር ምክንያት ወደ ሸዋ ለመሰደድ ተገደዋል። በዚህ ሳምንታትን በፈጀ ጉዞ አለቃ ተጠምቆን እየመሩ ደብረ ሊባኖስ ያደረሷቸው ደቂቁ ለማ ነበሩ።

እነዚህን ዘመን አይሽሬ ሊቃውንት ዲማ ጊዮርጊስ ላይ ያገናኛቸው የዕውቀት መሻት እንደነበር አለቃ ለማ ኃይሉ በመጽሐፈ ትዝታ መጽሐፋቸው፤ “በዘመኑ የነበሩትን ሰዎች የአካልና የመንፈስ ጽናት፣ ለዕውቀትም ሆነ ለወጠኑት ዓላማ የነበራቸውን እልህና ትዕግሥት፣ ችግርን መከራን የሚመክቱበት ጥንካሬና ብልሃት፣ እርስ በእርሳቸው የነበራቸውን ሁሉንም ዓይነት ሕይወት ግንኙነትና መስተጋብር ያመለክታል። ማህበረሰቡ እርስ በእርስ ተያይዞ፣ ተቻችሎና ተደጋግፎ ለዘመናት አብሮ እንዲኖር ያደረጉት፣ ከብሔራዊ መንግሥትና ከብሔራዊ ሰንደቅ ዓላማ በላይ የሆኑ እሴቶች እንደነበሩ ይዘከራል” በማለት ገልጸውታል።

ዲማ ጊዮርጊስ ያፈራቻቸው ሊቃውንት

ደብረ ድማሕ ያስተናግድ በነበረውን ትምህርት ጥራት፣ ልቀት አመልካችና አንፀባራቂ የሆኑ በርካታ ሊቃውንት ተገኝተዋል። ከእነዚህ መካከልም አባ ጲውሊ (የብሉይ እና የሐዲስ መምህር)፣ አባ ዝክረ (የሐዲስ እና መጥሐፈ ሊቃውንት መምህር)፣ እና አባ መዝሙረ ድንግል (የብሉይ መምህር) እንደ ምሳሌነት ሊወሰዱ ይችላሉ።

በቅርብ ዘመንም በጽሑፍ ሥራዎቻቸው በኢትዮጵያ የነበረው ሃይማኖታዊው እና ትውፊታዊው አመራር እንዲቀጥል ትልቅ ስራ የሰሩ በትውልድም ሆነ በትምህርት ዲማ ያፈራቻቸው ምሁራን ነበሩ። ከእነዚህ ምሁራን መካከል አንዱ መልዓከ ብርሃን አድማሱ ጀምበሬ ናቸው። ሊቁ አድማሱ ጀምበሬ ያበረከቱልን የሃይማኖት መጻህፍት ምክንያታዊ የሆኑ ክርክሮች፣ በተዋህዶ ኦርቶዶክሳውያን እምነት የዕውቀት ምንጮች እንደነበሩ ይታወቃል።

በመልዓከ ብርሃን አድማሱ ጀምበሬ የተዘጋጁት መጻሕፍት በጣም ብዙ ናቸው። በተለይም በቃል ይነገሩ/ ይነበነቡ የነበሩ ረቂቅ ቅኔዎችን በሁለት ቅፆች እንዲካተቱ በማድረግ፣ ሊረሱ ይችሉ የነበሩ የአገር ሃብቶቻችንን (ቅኔዎችን) ዘላለማዊ አድርገዋቸዋል። ስለሆነም የቅኔን እይታ እና ይዘት ከፍ ወዳለ ደራጃ አሸጋግረውታል።

እንዲሁም በኢትዮጵያ ዘመናዊ የሥነ ጽሑፍ ታሪክ ከፍተኛ ስፍራ ያላቸው ሀዲስ አለማየሁ ዲማ ጊዮርጊስ ካፈራቻቸው ሊቃውንት መካከል ይገኙበታል። ዲማን ማዕከል አድርጎ በተጻፈው በዝነኛው ድርሰታቸው፣ በ”ፍቅር እስከ መቃብር” በዘመኑ የነበረው ማህበራዊ ይዘት ምን እንደሚመስል በማሳየት ከፍተኛ የሆነ አይረሴ ትምህርት አበርክተውልናል።

በአንድ ወቅት በምሥራቅ ጎጃም ገድ አፋፍ ላይ የምትገኘዋን ዲማ ጊዮርጊስ ገዳምን ስጐበኝ የተሰማኝን ሃሳብ ከዓመታት በኋላ በአነስተኛ ስንኝ ለመግለጽ እንዲህ ሞክሬያለሁ፣

በዜማ ምሰሶ፣ በትርጉም ተማግራ፣

ገድ አፋፍ ላይ ቆማ፣ ቅኔ እም ታበራ፤

የሊቆች መስፈሪያ፣ እልፍኝ የነበረች፣

«አስኳላ» ገፍትሯት፣ ጋጥ ሆና ከረመች።

መደምደሚያ

ስለ ዲማ ጊዮርጊስ ነባራዊ ይዘት፣ የአስተዳደርም ሆነ የትምህርት ሥርዓት በቂ መረጃ አለኝ። ይህን መረጃ መነሻ አድርጌም በዲማ ጊዮርጊስ የነበረን ባህላዊ አስተዳደርና እና ትምህርት ነክ ይዘት ለመግለጽ ሞክሬያለሁ። የዚህ ጽሑፉ ዋና ዓላማ ደግሞ ቀደም ሲል የነበሩ ይዘቶችንና ሥርዓቶችን በማጥናት፣ በመመርመር፣ ለዘመናችን ሁኔታዎች፣ ችግሮች፣ የመፍትሄ ግብዓቶች ሊሆኑ የሚችሉ ተሞክሮዎችን ለአንባቢያን ማካፈል ነው። በመሆኑም ነባር እውቀትን፣ ተሞክሮን ያገናዘበ እቅድ ላይ ተመርኩዞ፣ የወደፊቱን እንቅስቃሴ፣ እርምጃ መተለም ብሎም መገንባት፣ ለግንባታው ጽናትን ይሰጣል የሚል እምንት ስላለኝ ተሞክሮውን ለማቅረብ ሞክሬያለሁ። በተጨማሪም ስለነበሩ መልካም ሥርዓቶች ማወቁ በራሱ መንፈሳዊ ሃሴት ያጎናጽፋል፣ ባህልንም ያዳብራል የሚል አመለካከት አለኝ።

ዘመን መጽሔት ሐምሌ 2014 ዓ. ም

ሽብሩ ተድላ (ፕሮፌሰር ኤሜሪተስ)



ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን

  የሊቃውንት መፍለቂያ! ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን በምሥራቅ ጎጃም ዞን ደብረ ኤልያስ ወረዳ የሚገኘው ደብረ ገነት ነብዩ ኤልያስ ቤተ ክርስቲያን በ15ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በአጼ ዘርዓ ያዕቆብ ዘመነ መንግሥ...